ኢትዮጵያውያን ታዳጊዎች ወደ ጄኔቫ ያመራሉ
የኢትዮጵያ ወጣቶችን የቴክኖሎጂ ባለቤትነትና የፈጠራ አቅም ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግረው “ሮቦቲክስ ለበጎ ዓላማ” (Robotics for Good Ethiopia 2026) ሀገራዊ ሻምፒዮና የእንቅስቃሴ መርሃ-ግብር በዛሬው ዕለት በይፋ ተጀምሯል።
በዓለም አቀፉ የቴሌኮሙኒኬሽን ህብረት (ITU) አዘጋጅነት የሚካሄደው ይህ ውድድር፤ ዕድሜያቸው ከ10 እስከ 18 የሆኑ ታዳጊዎች በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስና በሮቦቲክስ አማካኝነት ለዓለም አቀፍ ችግሮች መፍትሔ እንዲያመነጩ የሚያስችል ታላቅ መድረክ መሆኑ ተገልጿል።
የዘንድሮው ውድድር “የምግብ ዋስትና እና ዘመናዊ ግብርና” በሚል መሪ ቃል የሚካሄድ ሲሆን፣ ተወዳዳሪዎች በግብርናው ዘርፍ ያሉ ተግዳሮቶችን የሚቀንሱ ሮቦቶችን የመንደፍና የመገንባት ኃላፊነት ተሰጥቷቸዋል።
በማስጀመሪያ መርሃ-ግብሩ ላይ የተገኙት የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሰለሞን ሶካ፣ ውድድሩ ለሀገር በቀል የፈጠራ ሥራዎች መጎልበት ያለውን ፋይዳ አጽንኦት ሰጥተውበታል። ሀገራዊ የማጣሪያ ውድድሩም መጋቢት 19 ቀን 2018 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ሳይንስ ሙዚየም በደመቀ ሁኔታ እንደሚካሄድ ታውቋል።
በዚህ ሀገራዊ የፈጠራ ንቅናቄ በጁኒየር እና በሲኒየር ምድቦች አሸናፊ የሚሆኑት ሁለት ምርጥ ቡድኖች፣ በጄኔቫ ስዊዘርላንድ በሚካሄደው “AI for Good Global Summit 2026” ዓለም አቀፍ ውድድር ላይ ኢትዮጵያን ወክለው እንዲሳተፉ ሙሉ ወጪያቸው የተሸፈነ ጉዞና እውቅና ያገኛሉ።
ፕሮግራሙ በክልል ማጣሪያዎችና በቴክኒክ ስልጠናዎች ታጅቦ ዓመቱን ሙሉ የሚቀጥል ሲሆን፣ የግሉ ዘርፍና የሚዲያ ተቋማት ለዚህ ታላቅ ሀገራዊ ጥሪ አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል።
