በደቡብ ሱዳን መንግሥት ጦር እና በተቃዋሚዎች መካከል የሚደረገዉን ዉጊያ የሸሹ በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ የሐገሪቱ ዜጎች ምዕራብ ኢትዮጵያ ጋምቤላ ክልል መግባታቸዉን የክልሉ ባለሥልጣናትና የተባበሩት መንግሥታት የሥደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር (UNHCR) አስታወቁ።
ካለፈው መጋቢት ወር 2017 ዓ.ም ጀምሮ በደቡብ ሱዳን መንግሥት ጦርና በመንግሥት ተቃዋሚ ኃይሎች መካክል በተፈጠረው ጦርነት ምክንያት በርካቶች ወደ ኢትዮጵያ፣ ጋምቤላ ክልል ዋንታዋ ወረዳ መግባታቸውን የዋንታዋ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ጋትዊች ቡዝ ገልጸዋል።
“ለስደተኞቹ በቂ ምግብ እየቀረበላቸው አይደለም” ያሉት አስተዳዳሪው፤ በግምት የተመዘገቡና ያልተመዘገቡ 50ሺህ ያክል ስደተኞች ማታር እና ሙን በተሰኙ የወረዳው አካባቢዎች ህብረተሰቡ ያለውን እያካፈላቸው እየኖሩ እንደሆነ አክለዋል፡፡
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የስደተኞች ኮሚሽን (UNHCR) በዋናነት ሴቶችና ህፃናት የሚበዙባቸው ስደተኞች ድንበር አቋርጠው ወደ ኢትዮጵያ፣ ጋምቤላ ክልል፣ ዋንታዋ ወረዳ እንደገቡ ማረጋገጡን ዶቼ ቬለ ዘግቧል፡፡
ኮሚሽኑ ለጣቢያው በላከው ደብዳቤ እንዳሳወቀው ስደተኞቹ በድንገት አካባቢያቸውን በመልቀቃቸው ለምግብ እጥረት፣ ለህክማና እጦት፣ ለመጠለያና ለሌሎች ችግሮች የተጋለጡ እንደሆኑ ገልጧል፡፡
የሰደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት የጋምቤላ ቅርንጫፍ ኃላፊ አቶ መዝገበ ገብረማሪያም በበኩላቸው ደግሞ በደቡብ ሱዳን በነበረ ጦርነት 35ሺህ የሚገመቱ ስደተኞች በተለያዩ ጊዜዎች ወደ ጋምቤላ ክልል ዋንታዋ ወረዳ መግባታቸውን ጠቁመዋል፡፡
አክለውም እስካሁን ለተፈናቃዮች መጠለያ ካምፕ እንዳልተገነባ ጠቅሰው፤ አሁን ላይ ከጋምቤላ ክልል መንግሥት ለመጠለያ ግንባታ ቦታ “ሏክዶንግ” በተባለ አካባቢ መውሰዳቸውንና የግንባታ ቅደመ ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆናቸውን አመልክተዋል፡፡
በጋምቤላ ክልል በ7 የመጠለያ ጣቢያዎች ከ380ሺህ በላይ የደቡብ ሱዳን ተፍናቃዮች እንደሚኖሩ በዘገባው ተካቷል፡፡
