በትግራይ ክልል ሰለዋ፣ ሳምረ እና ሰየምቲ አድያቦ በተሰኙ ሶስት ወረዳዎች ላይ ባጋጠመ የኮሌራ ወረርሽኝ 161 ሰዎች የተጠቁ ሲሆን 46 ሰዎች በፅኑ መታመማቸውን የክልሉ የጤና ቢሮ አስታውቋል።
ብስራት ከትግራይ ክልል ጤና ቢሮ ያገኘው መረጃ እንደሚያሳየው ከሆነም ከአጠቃላይ ተጠቂዎቹ ሰባቱ የህክምና ክትትል እየተደረጋላቸው ሲሆን 149 ሰዎች በተደረገላቸው ህክምና አገግመው ወደ ቤታቸው ተሸኝተዋል።
ወረርሽኙ ባጋጠመባቸው ሶስቱ ወረዳዎች እስከ ነሀሴ 17 ቀን 2017 ዓ/ም ባለው ጊዜ ውስጥ በአጠቃላይ የአምስት ሰዎች ሞት መመዝገቡም የትግራይ ክልል ጤና ቢሮ አስታውቋል።
ከሟቾቹ መካከል ሁለቱ የሳምረ ነዋሪ የሆኑ አባት እና ልጅ ሲሆኑ ከአባትየው በተወሰደ ናሙና የተደረገ ምርመራ ኔጋቲቭ ሆኖ መገኘቱ ተገልፆል።
የግልና የአከባቢ ፅዳት አለመጠበቅ ዋንኛ የበሽታው መንስኤ ነው ያለው ቢሮው ማህበረሰቡ ግላዊና የአከባቢ ፅዳት መጠበቅ፣ የሚጠጣ ውሃ ብሎም ምግብ ፅዳት መጠበቅ፣ ሁልጊዜ መፀዳጃ ቤት መጠቀምና በአግባቡ ማፅዳት፣ እንዲሁም በወሳኝ ሰዓታት እጆችን በዉሃና በሳሙና በሚገባ መታጠብ ወረርሽኙን ለመግታት ቁልፍ መሆናቸው ብስራት ከትግራይ ክልል ጤና ቢሮ ያገኘው መረጃ አሳይቷል።
