ለተፈናቃዮች የመጀመሪያ ዙር ምግብ ነክ ያልሆነ ድጋፋ መደረጉ ተነግሯል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አሪ ዞን ደቡብ አሪ ወረዳ ኮመር ቀበሌ ሐምሌ 13 ቀን 2017 ዓ.ም በተከሰተው የመሬት መንሸራተት አደጋ ሕይወታቸውን ያጡ 5 የአንድ ቤተሰብ አባላት አስክሬን ተገኝቶ የቀብር ሥነ-ስርዓት መፈጸሙን፤ በኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማሕበር የክልሉ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ተስፋዬ ዱንዳ ተናግረዋል።
ከአደጋው ጋር በተያያዘም 1 ሺሕ 19 ነዋሪዎች ተፈናቅለው በድንኳን እና በሃይማኖት ተቋማት ውስጥ ተጠልለው እንደሚገኙ ኃላፊው ገልጸዋል፡፡
በክልሉ ከሚገኙ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶቹ ማለትም ከጎፋ፣ ወላይታና ጌዴኦ ቅርንጫፎች የተሰባሰበ ድጋፍ በቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ በኩል በቀጥታ ለተጎጂዎቹ መቅረቡንም አብራርተዋል።
በዚህም እንደ ቤት ውስጥ መገልገያ ቁሳቁሶች፣ የንጽህና መጠበቂያዎች፣ ብርድ ልብሶችና ሌሎች ድጋፎች ምግብ ነክ ያልሆኑ ቁሳቁሶች በአደጋው ለተፈናቀሉ ወገኖች መቅረባቸውን ጠቁመዋል።
አደጋው ከተከሰተበት ወቅት ጀምሮ አስክሬን በማፈላለግና አስፈላጊ ድጋፎችን በማቅረብና በማስተባበር ሰፊ ሰብዓዊ ድጋፎች ሲያደርጉ መቆየታቸውን ጠቅሰዋል።
በመጀመሪያ ዙር ከተደረገው ድጋፍ ባሻገር በቀጣይ ሌሎች መሰል ድጋፎችን በቀሪ ቅርንጫፎቹና በብሄራዊ ማህበሩ በኩል ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ገልጸዋል።
በዞኑ በአደጋው ጉዳት ለደረሰባቸው ሟች ቤተሰቦች ከሚሰጠው ድጋፍ በተጨማሪ ለተፈናቀሉ ዜጎች እየተደረገ ያለው ወገናዊ አጋርነት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም የቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ ተስፋዬ ዱንዳ አሳስበዋል
አሐዱ
