በህገ ወጥ መንገድ ሰነደ ሙዓለ ንዋዮችን ለህዝብ ሽያጭ በማቅረብ ገንዘብ ሲያሰባስቡ በነበሩ አቶ ኤርሚያስ አመልጋ እና “ጀነሲስ ኢንቨስትመንት ሰርቪስ” ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ላይ ምርመራ መጀመሩን የኢትዮጵያ የካፒታል ገበያ ባለስልጣን አስታወቀ ፡፡
ባለስልጣኑ በህገ ወጥ መንገድ ሰነደ ሙዓለ ንዋዮችን ለህዝብ ሽያጭ በማቅረብ ገንዘብ ሲያሰባስቡ በነበሩ ግለሰቦችና ድርጅቶች ላይ የቀረቡ ቅሬታዎችን ተቀብሎ ምርመራ እያደረገ እንደሚገኝ አስታውቋል ።
ከእነዚህ ቅሬታዎችም መካከል አቶ ኤርሚያስ አመልጋ እና “ጀነሲስ ኢንቨስትመንት ሰርቪስ” የተባለ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ሆኖ የተመዘገበ ኩባንያ ይገኙበታል።
ባለስልጣኑ ባወጣው መግለጫ ምርመራው የሚደረገው በኢ.ፌ.ዴ.ሪ ህገ መንግስት “የመሰማት መብት” መርህ መሰረት ሲሆን፤በህገ መንግስቱም ሆነ በሌሎች ህጎች የተሰጡ መብቶች እና ጥበቃዎች በሙሉ ይከበራሉ::
ግለሰቦች እና ድርጅቶች ከካፒታል ገበያ ጋር ተያያዥ የሆኑ እንቅስቃሴዎች ላይ ሲሳተፉ ተገቢ የሆኑ ጥንቃቄዎችን ማድረግ ይገባቸዋል።
በመሆኑም ባለስልጣኑ ግለሰቦችና ድርጅቶች በንግድ ድርጅቶች ምስረታ ላይ ሲሳተፉ ከንግድ ምዝገባ እና ከምስረታ ጋር የተያያዙ ሰነዶችን የመመዝገብ እና የማረጋገጥ ስልጣን ከተሰጣቸው አካላት ተገቢውን ማጣራት በማድረግ እንዲሁም ገንዘብ ከመክፈላቸውም በፊት በባለስልጣኑ ፈቃድ ከተሰጣቸው የኢንቨስትመንት አማካሪዎች ብቻ ምክር በመጠየቅ እንዲሆን ባለስልጣኑ መልዕክቱን አስተላልፏል ፡፡
ህብረተሰቡ የካፒታል ገበያ አገልግሎት ሰጪ ለመሆን ፈቃድ ለማውጣት በሂደት ላይ መሆናቸውን በመግለጽ ኢንቨስትመንት ከሚጠይቁ ግለሰቦች እና ድርጅቶች ጋር ውል ከመግባት እና ገንዘብ ከመክፈሉ በፊት በትክክል ለምዝገባ ማመልከት አለማመልከታቸውን ከኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን እንዲያጣራ እንዲሁም ፈቃድ አግኝተናል በሚል የሚንቀሳቀሱ ወይም የሚያስተዋውቁ ግለሰቦች እና ድርጅቶች ጋር ከመዋዋል እና ገንዘብ ከመክፈሉም በፊት ፈቃድ የተሰጣቸው መሆን አለመሆኑን ከባለስልጣኑ እንዲያረጋግጥ ባለስልጣኑ አሳስቧል ፡፡
ፈቃድ ሳይሰጣቸው የካፒታል ገበያ አገልግሎት የሚሰጡ፣ ለመስጠት የሚንቀሳቀሱ እና በማንኛውም ሚዲያ የሚያስተዋውቁ ግለሰቦች እና ድርጅቶች ካሉ ለባለስልጣኑ ጥቆማ እንዲሰጥ ያሳሰበ ሲሆን እንደዚህ ያሉ ግለሰቦች እና ድርጅቶች ላይ ባለስልጣኑ ተገቢውን እርምጃ እንደሚወስድ አስታውቋል ::
