የኢትዮጵያ የካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ለገዳ ሴኩዩሪቲስ ዲለር አ.ማ. (Gada Securities Dealer S.C.) የካፒታል ገበያ አገልግሎት ሰጪነት ፈቃድ መስጠቱን ተከትሎ፣ በአገሪቱ የሰነደ ሙዓለ ንዋይ ገበያ አከናዋኞች ቁጥር ወደ ሁለት ከፍ ማለቱ ተገለጸ።
ይህ አዲስ ፈቃድ የተሰጠው፣ ኢትዮ ፊደልቲ ሴኩዩሪቲስ የመጀመሪያው የሰነደ ሙዓለ ንዋይ ገበያ አከናዋኝ ፈቃድ ከተሰጠው ከአራት ወራት በኋላ ነው። ይህም በሀገሪቱ የካፒታል ገበያ ምስረታ ሂደት ውስጥ ሌላኛው ትልቅ ምዕራፍ ተደርጎ ተወስዷል።
ባለሥልጣኑ ዛሬ ረቡዕ ታኅሣሥ 15 ቀን 2018 ዓ.ም በይፋ በሰጠው የሥራ ፈቃድ፣ ገዳ ሴኩዩሪቲስ በሰነደ ሙዓለ ንዋይ ገበያ አከናዋኝነት ዘርፍ እንዲሰማራ ፈቅዶለታል።
ከዚሁ ጋር ተያይዞ የድርጅቱ የአራት ተሿሚ እንደራሴዎች ፈቃድ እና የስድስት የቦርድ አባላት ሹመት በባለሥልጣኑ መጽደቁ ታውቋል።
ይህ አዲስ ፈቃድ በአገሪቱ ውስጥ ፈቃድ ያገኙ ጠቅላላ የካፒታል ገበያ አገልግሎት ሰጪዎችን ቁጥር ወደ 14 ያሳደገው ሲሆን፣ በዘርፉ ያለውን ተወዳዳሪነትና ተደራሽነት ይበልጥ ያጠናክረዋል ተብሎ ይጠበቃል።
ባለሥልጣኑ እንደገለፀው ፤ እነዚህ ተቋማት ትክክለኛ የዋጋ ተመን እንዲኖር በማስቻልና የንግድ ልውውጥን በማሳለጥ ረገድ ሚናቸው የጎላ መሆኑን አመልክቷል።
