በኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት 2 ነጥብ 3 ሚሊየን ዜጎች ከስኳር ሕመም ጋር ይኖራሉ ሲል የኢትዮጵያ ስኳር ሕመም ማህበር ገለፀ።
የማህበሩ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጌታሁን ታረቀኝ÷ የስኳር ሕመም በዓለም አቀፍ ደረጃ ባለፉት ዓመታት በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋ መምጣቱን ገልፀዋል፡፡
በኢትዮጵያም በስኳር ሕመም የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ገልፀው÷ በተለይም ትክክል ባልሆነ የአኗኗር ዘይቤ ሳቢያ የሚከሰተው አይነት ሁለት የስኳር ሕመም እየተስፋፋ መምጣቱን አመልክተዋል፡፡
በዚህም በኢትዮጵያ እድሜያቸው ከ20 እስከ 79 ዓመት የሆኑ ከ2 ነጥብ 3 ሚሊየን በላይ ሰዎች ከስኳር ሕመም ጋር አብረው እንደሚኖሩ መረጃዎች ያመላክታሉ ሲሉ ተናግረዋል፡፡
አያይዘውም በአሁኑ ጊዜ ዝቅተኛ እና መካከለኛ ገቢ ባላቸው ሀገራት ውስጥ የስኳር ሕመም በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ መምጣቱ አሳሳቢ ያደርገዋል ያሉት ዶ/ር ጌታሁን÷ ወደፊትም የታማሚዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚጨምር መረጃዎች ያመላክታሉ ብለዋል፡፡
ጤናማ የሆነ የአኗኗር ዘይቤን በመከተል አይነት 2 የስኳር ሕመምን እስከ 80 በመቶ መከላከል እንደሚቻል ገልፀው የአካል ብቃት እንቅስቃሴ በማድረግ እና አመጋገብን ማስተካከል በተለይም ልጆች የሚመገቡትን በፋብሪካ የተቀነባበሩ ከፍተኛ የስኳርና ስብ መጠን ያላቸውን ምግቦች መቀነስ እንደሚገባ መግለጻቸውን የዘገበው ኤፍ ኤም ሲ ነው፡፡
