አስትሮፖርት ስፔስ ቴክኖሎጂስ እና አስትሮላብ የተባሉ የኢንጂነሪንግ ስታርት አፕ ኩባንያዎች በጨረቃ ላይ ለሚከናወን ግንባታ ተብሎ የተሰራውን “UTIPA Excavator” የተሰኘ ሙሉ በሙሉ በኤሌክትሪክ የሚሰራ የቁፋሮ ማሽን ሙከራ በስኬት ማጠናቀቃቸውን አስታውቀዋል።
ይህ ወሳኝ የሆነ የማሳያ መርሃ-ግብር ባለፈው ጥር ወር በሳን አንቶኒዮ በሚገኘው የአስትሮፖርት ዋና መሥሪያ ቤት ውስጥ መከናወኑን የኩባንያዎቹ መግለጫዎች አመልክተዋል።
ይህ ዘመናዊ የቁፋሮ ማሽን በጨረቃ ላይ የግንባታ ቦታዎችን ለማዘጋጀት እና ከ “Astrolab’s FLEX” ሮቨር ጋር በመቀናጀት ሰው አልባ በሆነ መንገድ የተለያዩ ተግባራትን ለማከናወን የተቀረጸ ነው።
የጨረቃ ላይ ቁፋሮ እና የግንባታ መሣሪያዎችን የሚያመርቱ ኩባንያዎች እንደሚገልጹት፣ በጨረቃ ላይ በብዛት ይገኛል ተብሎ የሚታሰበው “Helium-3” የተሰኘው የሂሊየም አይሶቶፕ ከፍተኛ ፍላጎት መኖሩ ለዚህ የጠፈር ላይ ግንባታና የሀብት ፍለጋ እንቅስቃሴ ዋነኛ አንቀሳቃሽ ምክንያት ሆኗል።
የአስትሮፖርት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሳም ዚሜኔስ እንደገለጹት፣ ይህ የቁፋሮ ማሽን ሙከራ ስኬታማ መሆን ቴክኖሎጂያቸው በንድፈ-ሐሳብ ደረጃ ብቻ ሳይሆን በተግባርም መሥራት የሚችል መሆኑን ያረጋገጠ ነው።
ይህ ግስጋሴ ወደፊት በጨረቃ ላይ ለሚገነቡ መሠረተ ልማቶችና ለጠፈር ምርምር አዳዲስ የሥራ ዕድሎችን የሚፈጥር መሆኑ ታምኖበታል።
