ባሕልና ስፖርት ሚኒስቴር የቡሔን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የትምህርት፣ ሳይንስና ባህል ተቋም (ዩኔስኮ) በማይዳሰሱ ቅርሶች ዝርዝር ውስጥ ለማስመዝገብ ባለሙያዎች መድቦ የሰነድ ዝግጅት ሥራ ማጠናከሩን አስታውቋል።
ተቋሙ ከቅርስ ባለሥልጣን ጋር የተቀናጀ ሥራ በመሥራት በዩኔስኮ ለማስመዝገብ ጥረት እየተደረገ መሆኑ ተገልጿል።
በባሕል እና ስፖርት ሚኒስቴር የባሕል እሴቶች እና ሀገር በቀል ዕውቀቶች ጥናት እና ልማት ባለሙያ አቶ ማተቤ ጥላሁን “ቡሔ ራሱን የቻለ ሃይማኖታዊ፣ ባሕላዊ እና ታሪካዊ ዳራ አለው” ብለዋል።
በዓሉ በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በልዩ ልዩ ክዋኔዎች እንደሚከበር ያስታወሱት ባለሙያው፤ የቡሔን ባሕላዊ ይዘት እና አጠቃላይ ክንዋኔዎች መሠረት ያደረገ መረጃ የመሰነድ ሥራ እየተከናወነ እንደሆነ ተገልጿል።
ቡሔ የአንድነት እና ተባብሮ የመኖር ማኅበራዊ መስተጋብር የሚታይበት እንደሆነ ተመላክቷል።
የገበያ ትስስር እና የዕደ ጥበብ ምርቶች ግብይትም ከበዓሉ እሴቶች መካከል ናቸው ተብሏል።
ዓመታዊውን ቡሔ በቅርስነት ጠብቆ ለቱሪዝም መስብነት ለማዋል የጋራና የቅንጅት ሥራ እንደሚያስፈልግ ተመላክቷል።
አሐዱ ሬዲዮ
