የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ ዛሬ ባካሄደው ግዙፍ የውጭ ምንዛሬ ጨረታ 500 ሚሊዮን ዶላር ለገበያ ያቀረበ ሲሆን፣ የቀረበው ፍላጎት ግን ካቀረበው በታች (455.29 ሚሊዮን ዶላር) ሆኖ ተመዝግቧል።
በዚህም ምክንያት በጨረታው የተሳተፉ 30 ባንኮች የጠየቁትን የውጭ ምንዛሬ ሙሉ በሙሉ ማግኘት ችለዋል።
በጨረታው አንድ ዶላር በአማካይ 153 ብር ከ25 ሳንቲም የተሸጠ ሲሆን፣ ከፍተኛው የመጫረቻ ዋጋ 154 ብር፣ ዝቅተኛው ደግሞ 152 ብር ሆኖ ተመዝግቧል።
ይህ የዛሬው ጨረታ ካለፈው ጥር ወር አፈጻጸም ጋር ሲነጻጸር መጠነኛ የዋጋ ቅናሽና የፍላጎት መረጋጋት የታየበት ነው። በጥር ወር በተደረገው ተመሳሳይ ጨረታ የአንድ ዶላር አማካይ ዋጋ 154 ብር ከ81 ሳንቲም የነበረ ሲሆን፣ በወቅቱ ከተሳተፉት 31 ባንኮች መካከል ዶላር ማግኘት የቻሉት 25ቱ ብቻ ነበሩ።
የዛሬው ውጤት ባንኮች የነበራቸው የውጭ ምንዛሬ ጥማት እየረገበ መምጣቱንና ብሄራዊ ባንክ ገበያውን ለማረጋጋት የያዘው ስትራቴጂ እየሰራ መሆኑን አመላካች ነው ተብሏል።
