በኢትዮጵያ የኮንስትራክሽንና የሪል እስቴት ኢንዱስትሪ ውስጥ ለሦስት አሥርተ ዓመታት ገደማ ስሙን የገነባው ጃምቦ ኮንስትራክሽን፣ አዲስ ወደ ገበያው በገባው ጀንቦሮ ሪል እስቴት ላይ የንግድ ምልክት ስያሜዬን ወስዶብኛል በሚል የ1 ሚሊዮን ብር የካሳ ክስ በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት መሰረተ።
ጃምቦ ኮንስትራክሽን ለፍርድ ቤቱ ባቀረበው አቤቱታ፣ “ጀንቦሮ” የሚለው ስያሜ ከራሱ የንግድ ምልክት ጋር በድምፅ፣ በፊደላት አጻጻፍና በቃና ተመሳሳይነት ስላለው ደንበኞችንና ሚዲያን እያደናገረ ይገኛል ብሏል። ድርጅቱ ይህን ድርጊት “የብራንድ ነጠቃ” ሲል የገለጸው ሲሆን፣ በዚህም ምክንያት 1 ሚሊዮን ብር የሚገመት የገንዘብ ኪሳራ እንደደረሰበት ገልጿል።
በሌላ በኩል ጀንቦሮ ሪል እስቴት ባቀረበው መከላከያ፣ ክሱ የሕግ መሠረት የሌለው ነዉ ሲል ተከራክሯል። ድርጅቱ አክሎም “ጀንቦሮ” የሚለው ስም በጉራጌ ዞን የሚገኝ የመንደር ስም እንጂ ከሱዋሂሊው “ጃምቦ” ጋር ምንም ዓይነት የቋንቋ ዝምድና እንደሌለው ገልጿል። የሪል እስቴት ደንበኞች ከፍተኛ ገንዘብ አውጥተው ከመግዛታቸው በፊት የድርጅቱን ማንነትና ታሪክ በሚገባ የሚመረምሩ በመሆናቸው፣ በስም ተመሳሳይነት ብቻ ይሳሳታሉ የሚለው ክስ ተቀባይነት የለውም ሲልም ጀንቦሮ ተከራክሯል።
