
የአሜሪካ እና ኢራን ፕሬዚዳንቶች ጦርነቱን ከአሁን ጀምሮ የሚያስቆመውን የመጀመርያ ስምምነት ፈረሙ።
ስምምነቱ የሆርሙዝ ወሽመጥን እንደገና መክፈት፣ የ300 ቢሊዮን ዶላር ኢራን “መልሶ የመገንባት” ዕቅድ፣ አሜሪካ ኢራን ላይ የጣለችውን “ሁሉንም ዓይነት ማዕቀቦች” የሚያስቆም ነው።
ነገር ግን የኢራን ጦርነት እንዲቀሰቀስ ዋነኛ ምክንያት የሆነው የኒውክሌር ፕርግራም ሊራዘም በሚችል 60 ቀናት ውስጥ ድርድር የሚካሄድበት ጉዳይ ሆኗል።
የአሜሪካውን ፕሬዚዳንት ፈረንሳይ በተካሄደው የቡድን ሰባት ጉባዔ ላይ በተሳተፉበት ወቅት ፊርማቸውን ሲያኖሩ “ምጣኔ ሃብታዊ ቀውስን” የሚያስቀር ዕቅድ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
ነገር ግን ከኢራን ጋር የመጨረሻው ስምምነት ላይ መድረስ ካልተቻለ “በቦምብ እንደበድባቸዋለን”ሲሉ ዝተዋል።
የኢራኑ ፕሬዚዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ረቡዕ ዕለት ስምምነቱ ላይ ፊርማቸውን ማኖራቸውን ቴህራን አረጋግጣለች።
የኢራን ቁልፍ ተደራዳሪ የሆኑት የምክር ቤቱ አፈ ጉባዔ ሞሃመድ ባግሃር ጋሊባፍ ለአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን አሜሪካ ላይ ያላቸው ጥርጣሬ እንዳለ መሆኑን አስታውቀው “ጣቶቻችን አሁንም ቃታ ለመሳብ ዝግጁ ናቸው” ብለዋል።
“ጠላት የተጠየቅነውን ቋንቋ ካልተረዳ ወደ ኃይል ቋንቋ ተመልሰን እንገባለን” ሲሉ ለፋርስ ኒውስ ተናግረዋል።
አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጦርነት የከፈተቱት የካቲት 21/2018 ዓ.ም. ነበር።
ሁለቱ አገራት ጥቃት በፈጸሙበት የመጀመርያ ቀን የአገሪቱ ጠቅላይ መሪን አያቶላህ አሊ ኻሜኒ እንዲሁም ከፍተኛ ወታደራዊ አመራሮች ተገድለዋል።
ነገር ግን ጦርነቱ ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ የሆርሙዝ ወሽመጥ ሙሉ በሙሉ በመዘጋቱ የዓለም ኤነርጂ ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ አሻቅቧል።
ትራምፕ በፈረንሳይ ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት ዕቅዱ ዓለም አቀፍ ድብታን ይቀለብሳል።
“የምጣኔ ሃብት ቀውስ ማየት አልፈልግም” ያሉት ትራመፕ “ጦርነቱ እንዲቀጥል የሚደረግ ከሆነ የሚከተለው ያ ነበር” ብለዋል።
