የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ቤንያሚን ኔታንያሁ በእስራኤል ወረራ ስር ያለው ዌስት ባንክን ወደ ግዛታቸው እንዲቀላቀሉ አልፈቅድም አሉ።
የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር አርብ ዕለት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ንግግር ከማድረጋቸው ቀደም ብለው በኦቫል ኦፊስ ለጋዜጠኞች ሃሳባቸው የሰጡት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት፤ “እስራኤል ዌስት ባንክን እንድትቀላቀል አልፈቅድም…አይሆንም” ብለዋል።
ሰኞ ከኔታንያሁ ጋር የሚገናኙት ትራምፕ የጋዛ ስምምነት “በጣም ተቃርቧል” ሲሉ ገልጸዋል።
እስራኤል በጋዛ ያለውን ጦርነት እና የዌስት ባንክን ወረራ እንድታቆም ዓለም አቀፍ ጫና እየደረሰባት ነው።
የምዕራባውያን መንግሥታት ለፍልስጤም ነጻ አገርነት በይፋ ዕውቅና እየሰጡ ነው።
ቀኝ ዘመም እስራኤላውያን አካባቢውን መጠቅለል ይህንን ግፊት ለማስቆም አማራጭ መንገድ እንደሆነ ይመለከቱታል።
