የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “በኢራን ላይ የሚወሰደው መጠነ ሰፊ ወታደራዊ እርምጃ” እንደሚቀጥል አስታወቁ።
የኢራን መንግሥት የኒውክሌር የጦር መሣሪያ ግንባታ እንዲያቆም ከአሜሪካ የተሰጠውን ማስጠንቀቂያ ችላ እንዳለም ገልጸዋል። ከቴህራን የተደቀነውን አደጋ ለመቀልበስ እርምጃ መውሰድ እንደሚቀጥሉም ተናግረዋል።
ለአሜሪካ ወታደሮች ሜዳልያ ለመስጠት በተዘጋጀ ሥነ ሥርዓት ላይ ንግግር ያደረጉት ትራምፕ “የኢራን የሚሳዔል መርሃ ግብር የኒውክሌር ግንባታን ለመሸፈን ያለመ ነበር” ሲሉም ተደምጠዋል።
ኒውክሌር የጦር መሣሪያ እና የረዥም ርቀት ሚሳዔል የታጠቀ የኢራን መንግሥት መካከለኛው ምሥራቅ እና የአሜሪካ ሕዝብ “ሊታገሱት የማይገባ ስጋት ነው” ብለዋል።
በኢራን ላይ እየወሰዱ ያሉት እርምጃ አላማው የአገሪቱን “የሚሳዔል ግንባታ አቅም እንዲሁም የባሕር ኃይል ማምከን” መሆኑን ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል።
“በተገደሉት የአሜሪካ ወታደሮች ስም ዘመቻውን አጠናክረን እንቀጥላለን” ብለዋል።
በኢራን ላይ እየተካሄደ ያለው ዘመቻ አሜሪካ ከያዘችው የጊዜ ሰሌዳ “በጣም እንደቀደመ” ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል።
ዘመቻው ከመነሻው ላይ ከአራት እስከ አምስት ሳምንት እንደሚወስድ እንደተገመተ የጠቀሱት ትራምፕ “ከዚያም በላይ የመዝለቅ አቅም አለው” ሲሉ ተናግረዋል።
