አሜሪካ በሚቀጥሉት ጥቂት ወራት ውስጥ በሶሪያ የቀሯትን ወታደሮች ለማስወጣት በዝግጅት ላይ መሆኗን አንድ ከፍተኛ የዋይት ሐውስ ባለሥልጣን ለቢቢሲ ተናገሩ።
ባለሥልጣኑ እንዳሉት የሶሪያ መንግሥት በግዛቱ ውስጥ ሽብርተኝነትን በመዋጋት ረገድ የመሪነት ሚናውን ለመጫወት እና የአሜሪካ ወታደራዊ ኃይል “በከፍተኛ ቁጥር” መኖሩ አስፈላጊ እንዳልሆነ ከስምምነት ላይ ተደርሷል።
የአሜሪካ ወታደሮች እአአ ከ2015 ጀምሮ በሶሪያ ውስጥ የሚገኙ ሲሆን ይህም የኢስላሚክ ስቴት ቡድን (አይኤስ) ተጽዕኖን ለመግታት የሚደረገው የፀረ-ሽብር ዘመቻ አካል ነበር።
የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሱት በመካከለኛው ምሥራቅ አገራቸው ከኢራን ጋር የገባችው ውጥረት እየተካረረ በመጣበት ወቅት ነው። ዶናልድ ትራምፕ ከዚህ ውሳኔያቸው በተቃራኒ በኢራን አቅራቢያ የአሜሪካ ጦር ኃይልን እያሰፈሩ ይገኛሉ።
ቢቢሲ ቬሪፋይ በኢራን አቅራቢያ የጦር ጄቶችን መሸከም የሚችለው የዩኤስኤስ አብርሃም ሊንከን መርከብ መኖሩን አረጋግጧል።
ባለሥልጣኑ እንዳሉት ወደ 1,000 የሚጠጉ የቀሩትን ወታደሮች ከሶሪያ የማስወጣት ውሳኔ የአገሪቱ አስተዳደር ሽግግር አካል ሲሆን አሜሪካም በቀጠናው ውስጥ ለሚከሰቱ ማናቸውም ስጋቶች ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ ሆና ትቀጥላለች።
የአሜሪካ ወታደሮች በዚህ ዓመት መጀመሪያ ላይ በሶሪያ ከሚገኙ ሁለት የጦር ሰፈሮች ለቅቀው ወጥተዋል።
ጦሩ ይህንን እርምጃ የወሰደው እአአ በ2024 የአሳድ መንግሥት መውደቁን ተከትሎ በሶሪያ ከፍተኛ የጸጥታ መሻሻል በመታየቱ እና ኢስላሚክ ስቴት መዳከሙን ተከትሎ ነው።
ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የትራምፕ አስተዳደር ከደማስቆ ጋር ያላቸውን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ለማጠናከር እና ከሶሪያ ፕሬዝዳንት አህመድ አል ሻራ ጋር ያላቸውን አጋርነት ለማሳደግ ጥረት አድርገዋል።
የሶሪያው ፕሬዚዳንት አህመድ አል ሻራ በኅዳር ወር ትራምፕን በዋይት ሐውስ አግኝተው የተወያዩ ሲሆን ይህም በሶሪያ ታሪክ የመጀመርያው ፕሬዚዳንት ያደርጋቸዋል።
