በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ማሲንጋ በቅርቡ ከድሮን ጥቃት ጋር በተያያዘ ኤምባሲያቸው ያወጣው መግለጫ “በስህተት ነው” ሲሉ ገለጹ
በኢትዮጵያ የአሜሪካን አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ኤምባሲያቸው ግንቦት 15 ቀን 2017 ዓ.ም “የፌደሬል መንግስት በዜጎቹ ላይ የሚፈጽመውን የድሮን ጥቃት በአስቸኳይ እንዲያቆም” በሚል የተላለፈው መልዕክት በስህተት ነው ሲሉ ገለጹ፤ መልዕክቱ “በአስተዳደራዊ ስህተት” የተካተተ ነበር ሲሉ በምክንያትነት አስቀምጠዋል።
“ስህተት ነበር፤ ስህተት ነበር ከማለት ውጭ ምንም ተጨማሪ የሚገለጽም ይሁን የሚቀነስ ነገር የለውም በመጀመሪያ የተጻፈውን የመግለጫውን ረቂቅ ነበር የተጠቀሙት፤ እኔ ያላየሁት እና ያላፀደኩትን ነው የተጠቀሙት፤ ይህም በአስተዳደራዊ ችግር የተፈፀመ እና እንዳለመታደል ሁኖ ተላለፈ” ሲሉ ዛሬ ሰኔ 5 ቀን 2017 ዓ.ም በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ተናግረዋል።
በመጀመሪያ ኤምባሲያቸው ያሰራጨው መረጃ “የፌደሬል መንግስት በዜጎቹ ላይ የሚፈጽመውን የድሮን ጥቃት በአስቸኳይ እንዲያቆም” የሚል ሀሳብ የነበረው ቢሆንም ከሰአታት በኋላ ይህ ሀሳብ እንዲነሳ ተደርጓል።
አምባሳደሩ በዛሬው መግለጫቸው በኤምባሲያቸው በኩል በኢትዮጵያ ለሚንቀሳቀሱ ታጣቂ ሀይሎች ለቀረበው የሰላማዊ ውይይት ጥሪ አስመልክተው በሰጡት አስተያየት “ከተወሰኑ የኦሮሞ ነጻነት ተዋጊ ቡድኖች እና ከአንዳንድ የፋኖ ታጣቂ ቡድኖች” በኩል አወንታዊ ምላሽ ማግኘቱን እና ተስፋ እንዳላቸው አስታውቀዋል፤ “በእርግጥ ብዛት ያላቸው እና ዘርዘር ያሉ ቅድመ ሁኔታዎችን አቅርበዋል” ብለዋል።
