የአሜሪካ መንግሥት ኢትዮጵያን ጨምሮ በአንዳንድ ሀገራት ላይ ተግባራዊ የሚያደርገው የቪዛ ዋስትና የሙከራ መርሃ ግብር ከመጪው መጋቢት 24 ቀን 2018 / April 2, 2026 ጀምሮ በይፋ እንደሚጀምር በኢትዮጵያ የአሜሪካ ኢምባሲ አስታውቋል።
ይህን አስመልክቶም አመልካቾች ከማጭበርበር እንዲጠበቁ ኤምባሲው ጥብቅ ማሳሰቢያ ሰጥቷል። በዚህም “አስቀድሞ መክፈል ቪዛ ለማግኘት ዋስትና አይሆንም” ሲል ነው ያስጠነቀቀው።
አክሎም ከቃለ-መጠይቅ በፊት የሚፈጸም ማንኛውም ክፍያ ተመላሽ አይደረግም ያለ ሲሆን ክፍያውን ለማስፈጸም የሚጠይቁ የሦስተኛ ወገን ድረ-ገጾች አጭበርባሪ ሊሆኑ ስለሚችሉ ተገቢውን ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋልም ብሏል።
ይህ የዋስትና ክፍያ ከመጋቢት 24 ቀን 2018 ዓ.ም / April 2, 2026 በፊት የተሰጠ ሕጋዊ የንግድ ወይም የቱሪስት (B1/B2) ቪዛ ያላቸውን ሰዎችን እና በኤፍ (F) ወይም ኤም (M) ቪዛ ወደ አሜሪካ የሚጓዙ ተማሪዎችን አይመለከትም ተብሏል።
