አዋሽ ባንክ እና ሳፋሪኮም ኤም ፔሳ (M-PESA ETHIOPIA SC) “እርፍ በኤምፔሳ” የተሰኘ መተግበሪያ በማስጀመር፤ በዲጂታል ቁጠባ እና ብድር አገልግሎት ዙሪያ አብሮ ለመስራት የሚያስችላቸውን የስታራቴጂክ አጋርነት ውል ዛሬ ሐምሌ 7 ቀን 2017 ዓ.ም በባንኩ ዋና መስሪያ ቤት ተፈራርመዋል።
የአዋሽ ባንክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፀሀይ ሽፈራው በፊርማ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንደተናገሩት፤ በዛሬው ዕለት ባንኩ ከኤም ፔሳ ጋር በተደረገው “እርፍ በኤምፔሳ” የተስኘው ዲጂታል የብድር አገልግሎት መተግበሪያ ስምምነት መሠረት ለደንበኞች የዲጂታል አነስተኛ ብድር አገልግሎት ለመስጠት አስፈላጊ ዝግጅት ተጠናቋል፡፡
በዚህም ባንኩ በመተግበሪያው ላይ የቴክኖሎጂ ማሻሻያዎችን እና ትስስሮችን በማድረግ ከመቼውም ጊዜ በላይ በተሻለና በላቀ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማከል ወደ ደንበኞቹ ለማቅረብ መዘጋጀቱን ተናግረዋል፡፡
አክለውም አጋርነቱ የአዋሽ ባንክን የፋይናንስ ጥንካሬ እና እምነት ከኤም-ፔሳ የቴክኖሎጂ ፈጠራ እና የሞባይል ገንዘብ አመራር ስርዓት ጋር በማገናኘት፤ በሚሊዮን ለሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ዲጂታል ብድር ለማቅረብ እንደሚያስችል ገልጸዋል።
የዚህ ዲጂታል አነስተኛ ብድር ተጠቃሚዎች በቀላሉ በእጅ ስልኮቻቸው ፈጣን አገልግሎት ወዲያውኑ እንደሚያገኙ ሁኔታዎች መመቻቸታቸውንም አክለው ተናግረዋል።
የM-PESA ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኤልሳ ሙዞሊኒ በበኩላቸው፤ “ለረጅም ጊዜ የኢትዮጵያ የፋይናንስ ሥርዓት ምሰሶ ከሆነው አዋሽ ባንክ ጋር በመተባበር የደንበኞቻችንን የፋይናንስ ደህንነት ለማሻሻል ያለው ዕድል ከፍተኛ ነው” ያሉ ሲሆን፤ “ይህንን ራዕይ ዕውን ለማድረግ የምንችለው እንደ አዋሽ ባንክ ካሉ ተቋማት ጋር በጠንካራ አጋርነት በመስራት ብቻ ነው” ብለዋል ።
የመጀመሪያ የዲጅታል ብድር ምርት በሆነው “እርፍ በኤምፔሳ” የደንበኞችን የብድር ግብይት ለማስፋፋት ብቻ ሳይሆን የደንበኞችን ቁጥር ለመጨመር የሚያስችል ትልቅ ዕድል እንዳለውም ገልጸዋል።
በተጨማሪም “በመረጃ ላይ የተመሰረተ ብድር ለመስጠት የሚያስችል እና ይህም የደንበኞችን የብድር ባህሪ የበለጠ ለመረዳት የሚያግዝ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።
አገልግሎቱ አሁን ለሁሉም የኤም ፔሳ ደንበኞች ለ90 ቀናት የቀረበ ተደራሽ፣ ቀላል፣ ደህንነቱ የተጠበቀ እና ፈጣን ዲጂታል የብድር አገልግሎት ሲሆን፤ በተለይም እያደገ የመጣውን የአነስተኛ ቢዝነሶችን፣ የቤተሰብ ኃላፊዎችን እና መደበኛ ያልሆኑ ነጋዴዎች የፋይናንስ ፍላጎት ለማሟላት ያለመ ነው ተብሏል፡፡
(አሐዱ ሬዲዮ)
