በአዲስ አበባ ከተማ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥን በእጅጉ የሚቀርፍ 232 ነጥብ 84 ኪ.ሜ የሚረዝም የነባር ኤሌክትሪክ መስመሮች የመልሶ ግንባታና የአዲስ መሰረተ ልማት ማስፋፋያ ስራ በተገባደደው የመጀመሪያ ሩብ ዓመት መጠናቀቁን በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የአዲስ አበባ ሪጅን ኦፕሬሽን ኮርዲኔሽን ጽ/ቤት አስታወቀ፡፡
ከተከናወነው የኤሌክትሪክ መስመር መልሶ ግንባታና የማስፋፊያ ስራ 105 ነጥብ 38 ኪሜ የነባር ኤሌክትሪክ መስመር የመልሶ ግንባታና የአቅም ማሳደግ ሲሆን፤ 127 ነጥብ 46 ኪ.ሜ ደግሞ የአዲስ መስመር ማስፋፋያ ይገኝበታል፡፡
ከፍተኛ የሆነ የኃይል ፍላጎት ባለባቸው አካባቢዎች የ130 ትራንስፎርመሮችን አቅም በማሻሻል፣ 210 አዳዲስ ትራንስፎርመሮችን በመትከል ለከተማው አስተማማኝ የኃይል አቅርቦት እንዲኖርና የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥን ለመቀነስ የሚያስችሉ ስራዎችም በሩብ ዓመቱ ተሰርቷል፡፡
3 ሺህ የሚሆኑ ለኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ምክንያት የሆኑ ግኝቶች ላይ የማስተካከያ (የቅድመ ጥገና) ሥራ ለመስራት ታቅዶ፤ በ2 ሺህ 914 ግኝቶች ላይ የማስተካከል (የቅድመ ጥገና) ሥራ ተከናውኗል፡፡
በአዲስ አበባ ካሉት 36 መጋቢ የምድር ስር ተቀባሪ መስመሮች መካከል 24 የምርመራ ስራ ተሰርቶላቸው ጥገናቸው የተጠናቀቀ ሲሆን፤ ቀሪዎቹ 12 መጋቢ መስመሮች በሁለተኛው ሩብ ዓመት ለማጠናቀቅ እየተሰራ ይገኛል፡፡
ከትራንስፎርመሮች ምርመራ ጋር በተያዘዘ የሩብ ዓመቱ መባቻ ድረስ 13 ሺህ 205 ትራንስፎርመሮችን ለመመርመር ታቅዶ ፤ 12 ሺህ 702ቱ ላይ ምርመራ ተደርጎ የጥገና ስራዎቹ በመሰራት ላይ ይገኛሉ፡፡
የአዲስ አበባ ሪጅን ማስተባበሪያ 31 የኃይል ማከፋፈያ ጣቢያዎችን (ሰብስቴሽን) ተጠቅሞ በተለያዩ የታሪፍ መደብ ያሉ ከ1 ሚሊየን 55 ሺህ በላይ ለሆኑ ደንበኞች አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት
