የኢትዮጵያ ፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ባካሄደው ጥናት መሰረት፣ የከሰምና የተንዳሆ የስኳር መስኖ ልማት ፕሮጀክቶች በሚፈለገው ደረጃ ባለመስራታቸው ሀገሪቱ በየዓመቱ 43 ቢሊዮን ብር እያጣች መሆኑን ገልጿል ።
የኢንስቲትዩቱ የግብርና እና ገጠር ልማት ተመራማሪ መኮነን በቀለ (ዶ/ር) ባቀረቡት ጥናት እንዳመለከቱት፣ በእነዚህ ፕሮጀክቶች መሬት ያለማሳካት፣ በግጭትና በተለያዩ ችግሮች ስራ መቆም እንዲሁም የጥገና መጓተት ከፍተኛ የገቢ እጥረት አስከትሏል።
በተለይም የከሰም ፕሮጀክት ከታቀደው 20,700 ሄክታር ውስጥ እየለማ ያለው 2,000 ሄክታር ብቻ በመሆኑ በዓመት 10 ቢሊዮን ብር ገቢ እንዳይገኝ ሆኗል ሲል ኢፕድ ዘግቧል።
በተንዳሆ ፕሮጀክት ደግሞ ከ9 ዓመታት በላይ ስራ በመቆሙ በዓመት 33 ቢሊዮን ብር ኪሳራ እየደረሰ መሆኑንና የአሌወሮ እንዲሁም ጎዴ ፕሮጀክቶችም ሙሉ አቅማቸው ባለመስራታቸው በዓመት 5.1 ቢሊዮን እና 6 ሚሊዮን ብር ገቢ እያጣች መሆኑንም ተጠቁሟል።
