የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይ.ኤም.ኤፍ) በጋራ ባካሄዱት አዲስ ግምገማ፣ ኢትዮጵያ ዕዳ የመክፈል ጫና ውስጥ መሆኗን አስታወቁ። ሪፖርቱ፤ ሀገሪቱ “ያልተረጋጋ የመበደር እና ዕዳ የመመለስ አቅም ላይ ናት” ሲል በመግለጽ፤ በኢኮኖሚ ላይ ጥብቅ ማሳሰቢያ ሰጥቷል።
በሁለቱም ተቋማት ከፍተኛ ባለሥልጣናት የጸደቀው ሪፖርቱ፣ “ኢትዮጵያ ከኤክስፖርት የምታገኘው ገቢ በቂ ባለመሆኑ ዕዳዋን የመመለስ አቅሟ የተዳከመ ነው” ብሏል። አክሎም፣ ሀገሪቷ የቦንድ ሽያጭ ክፍያዋን መክፈል ካልቻለችበት ታኅሣሥ 2023 ጀምሮ በዕዳ ጫና ውስጥ መሆኗን ገልጿል።
የተቋማቱ ግምገማ፤ የኢትዮጵያን የዕዳ መክፈል ችግርን ያባባሰው በአጭርና መካከለኛ ጊዜ ውስጥ የሚከፈል የዕዳ መጠን መብዛት እና በትግራይ ጦርነት ወቅት እና ከጦርነቱ በኋላ ከውጭ የሚገኝ የገንዘብ ድጋፍ በከፍተኛ ሁኔታ መቀነሱ መሆኑን አመላክቷል።
ሪፖርቱ፤ “የማሻሻያ አጀንዳ በወቅቱ መተግበር እና ከውጭ አበዳሪዎች የሚገኝ የዕዳ እፎይታ የገንዘብ እጥረትን ለማቃለል እና የዕዳዋን ለመቆጣጠር ይረዳል” ብሏል።
