የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለአንድ ወር ሲያካሄድ የቆየውን የመራጮች ምዘገባ በሁለት ሳምንት አራዘመ። ቦርዱ ጊዜውን ያራዘመው፤ በዲጂታል እገዛ ሲከናወን በቆየው ምዝገባ በተፈጠሩ ተግዳሮቶች እና በትራንስፖርት አቅርቦት ችግር የባከነውን ጊዜ ለማካካስ እንደሆን አስታውቋል።
ምርጫ ቦርድ ባለፈው ህዳር ወር ባወጣው የጊዜ ሰሌዳ፤ የመራጮች ምዝገባ ለማከናወን አቅዶ የነበረው ከየካቲት 7 እስከ መጋቢት 7፤ 2018 ነበር።
ሆኖም ቦርዱ በጊዜ ሰሌዳው መሰረት ያቀዳቸውን ስራዎች “አከናውኖ መጨረስ ባለመቻሉ”፤ የመራጮች ምዝገባ መጀመሪያው በሁለት ሳምንት እንዲገፋ አድርጓል።
በቦርዱ ውሳኔ መሰረት የካቲት 26 የተጀመረው የመራጮች ምዝገባ እንዲጠናቀቅ ቀነ ገደብ የተቀመጠለት ከአንድ ወር በኋላ ነበር። ቀነ ገደቡ ከመጠናቀቁ አራት ቀናት በፊት በጠቅላላ የተመዘገበው መራጭ ብዛት 36.9 ሚሊዮን መሆኑን ምርጫ ቦርድ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ መጋቢት 24 ባሰራጨው መረጃ አመልክቷል።
