የአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒን መግደሉን ተከትሎ የአገሪቶ ጦር፤ “እጅግ አስከፊ” የሆነ የአጸፋ እርምጃ እንደሚወስድ አስጠንቅቋል። ባለፉት ሰዓታት ከኢራን ጦርነት ጋር የተያያዙ በርካታ ክስተቶች ተፈጥተዋል፤ ዋና ዋናዎቹ እነዚህ ናቸው፦
- አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ቢሮቸው ውስጥ መገደላቸውን የኢራን የመንግሥት ቴሌቪዥን ዘግቧል። አገሪቱን ለ37 ዓመታት የመሩት ጠንካራውን የሃይማኖት መሪ የተገደሉባት ኢራን የ40 ቀናት ብሔራዊ ሐዘን አውጃለች።
- የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ለመሪው መገደል አጻፋ የሚሆን “አስከፊ ጥቃት” በአሜሪካ የጦር ሰፈሮች እና በእስራኤል ላይ እንደሚፈጽም አስጠንቅቋል።
- በኢራን ሕገ መንግሥት መሠረት የአያቶላህ አሊ ኻሜኒ ተተኪ የሚመረጠው እርሳቸውንም እዚህ ሥልጣን ላይ በሾማቸው የአመራር ሊቃውንት ጉባኤ ነው።
- ጥቃቱ ከተፈጸመ እና የኻሜኒን ሞት ከተረጋገጠ በኋላ አንዳንድ ኢራናውያን ደስታቸውን ሲገልጹ የታዩ ሲሆን ሌሎች ደግሞ ሐዘን ላይ ናቸው።
- የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው አያቶላህ ኻሜኒ፤ ”በታሪክ ከታዩ እጅግ ክፉ ሰዎች አንዱ” ነበሩ ብለዋል። የኻሜኒ ሞት፤ “የኢራን ሕዝብ አገሩን መልሶ ለመያዝ የሚያስችለው ብቸኛው ታላቅ ዕድል” እንደሆነም ገልጸዋል።
- የቀይ ጨረቃ መረጃ እንደሚያመለክተው ኢራን ውስጥ በተፈጸመው ጥቃት ከ200 በላይ ሰዎች ተገድለዋል። በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ‘ሲቢኤስ ኒውስ’ በበኩሉ 40 ገደማ የኢራን ባለሥልጣናት መሞታቸውን ዘግቧል።
- ኢራን፤ በመካከለኛው ምሥራቅ ባሉ የአሜሪካ አጋሮች ላይ እና የአሜሪካ የጦር ሰፈሮች በሚገኙባቸው ቦታዎች ላይ ጥቃቶችን ፈጽማለች። ጥቃቱ ከተሰነዘረባቸው መካከል፤ ዱባይ፣ ዶሃ፣ ባህሬን እና ኩዌት ይገኙበታል።
- በዓለም ላይ እጅግ በርካታ በረራዎችን ከሚያስተናግዱ የአቪዬሽን ማዕከላት አንዱ በሆነው በዱባይ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ እንዲከሽፍ የተደረገ ኢራን የሚሳዔል ስብርባሪዎች ወድቆ አራት ሰዎች እንደቆሰሉ የአገሪቱ መንግሥት አስታውቋል።
- የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር በበኩላቸው፤ ብሪታንያ ዜጎቿን እና ቀጣናዊ አጋሮቿን ለመጠበቅ ስትል “የተቀናጀ የቀጣናዊ የመከላከል ዘመቻ” ውስጥ እየተሳተፈች መሆኑን አስታውቀዋል።
