የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ በቅድመ ወንጀል መከላከል በጥናት ላይ ተመስርቶ ባማናወነው ክትትል ግለሰቦቹ በቁጥጥር ስር ውለዋል።
ነሐሴ 10 ቀን 2017 ዓ/ም ከቀኑ 7፡40 ሠዓት በጉለሌ ክ/ከተማ ወረዳ 8 ልዩ ቦታው አጂብ ቶታል ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ከሚገኝ አንድ መኖሪያ ቤት ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ጋር በተደረገ ፍተሻና ብርበራ ከ100 ኪሎ ግራም በላይ ካናቢስ የተሰኘን አደንዛዥ ዕፅ በቁጥጥር ስር ሊያውል መቻሉን አስታወቀ፡፡
ተጠርጣሪዎቹ አሸብር መኮንን እና ስብሀቱ አያሌው የሚባሉ ሲሆኑ የተጠቀሰውን አደንዛዥ ዕፅ አምስት አምስት ኪሎ በሚይዡ ከረጢቶች በመጠቅለል ወደ ገበያ ለማቅረብ ሲያዘጋጁ እንደተያዙም ፖሊስ አስታውቋል፡፡
ፖሊስ በተጠርጣሪዎቹ ላይ ተጨማሪ ምርመራ የማስፋት ተግባሩን አጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን ተገቢውን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎችን በማጠናቀር ክስ እንደሚያስመርትም ገልጿል፡፡
አደንዛዥ ዕፆችችን ማምረት፣ መስራት፣ ማዘዋወር ወይም መጠቀም የወንጀል ተጠያቂነትን እንደሚያስከትል በኢ.ፌ.ዲ.ሪ የወንጀል ህግ አንቀፅ 525 ላይ በግልፅ የተደነገገና በወንጀል የሚያስጠይቅ ተግባር መሆኑን ሁሉም ልብ ሊለው የሚገባ ከመሆኑም በላይ እነዚህን እና መሰል ዕፆችን ሲጠቀም፣ ሲያዘዋውር፣ ሲሸጥና ሲጠቀም የሚገኝ ማንኛውም ግለሰብም ይሁን ቡድን ላይ በህጉ መሰረት ጠበቅ ያለ ርምጃ እንደሚወስድም የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ ያሳስባል፡፡
ምንጭ:- አአ ፖሊስ
