የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን አዲሱ በጀት ዓመት ከገባ ጀምሮ በከተማዋ በሚገኙ 85 ተቋማት ላይ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ እርምጃ መውሰዱን አስታውቋል።
የባለሥልጣኑ የምግብና ጤና ነክ ቁጥጥር ዳይሬክተር አቶ እስጢፋኖስ ጌታቸው እንደተናገሩት፣ እርምጃው የተወሰደው በአያያዝ ችግር ምክንያት የተበላሹ ወይም ጊዜ ያለፈባቸው ምርቶችን ሲሸጡ በተገኙ ተቋማት ላይ ነው።
በዚህም መሰረት በተለያዩ ሱቆች እና ምግብና መጠጥ አቅራቢ ተቋማት ላይ የመሸግ፣ የህገወጥ ምርቶችን የማገድና ማስጠንቀቂያ የመስጠት እርምጃዎች ተወስደዋል። ከ85ቱ ተቋማት ውስጥ በተለይ 6ቱ ላይ ሙሉ በሙሉ የማሸግ እርምጃ የተወሰደ ሲሆን፣ እነዚህ ተቋማት በቀጣይ ተጨማሪ ቅጣት እንዲጣልባቸው ለሚመለከተው አካል መተላለፋቸውም ተገልጿል።
አቶ እስጢፋኖስ አክለውም፣ በህገወጥ መንገድ እርድ ሲያከናውንና ስጋ ሲያከፋፍል በነበረ አንድ ተቋም ላይ ከፌደራል ፖሊስ ጋር በመተባበር ክትትል ከተደረገ በኋላ ከ200 ሺህ ብር በላይ የሚያወጣ ስጋ ተወርሶ ወደ ቄራዎች እንዲገባ ተደርጓል።
ዳይሬክተሩ እንዳመለከቱት፣ ለበዓል ከሚደረገው መደበኛ ቁጥጥር በተጨማሪ አዲስ አበባ በምታስተናግዳቸው ዓለም አቀፍ ጉባኤዎች ምክንያት ዘንድሮ ልዩ ጥብቅ ቁጥጥር እየተደረገ ነው።
(መናኸሪያ ሬዲዮ)
