ሥዕል ያለፉ ታሪኮች፣ ባህል፣ አሁናዊ አኗኗር፣ ቋንቋን ስነ-ጥበባዊ በሆነ መንገድ የመግለጽ አቅም እንዲሁም ወደፊት ሊሆን ይችላል ተብሎ የሚታሰብን ሁነት በመተንበይ የማሳየት አቅም አለው።
በርካቶችም በስዕል ሥራዎቸው የአገራቸውን ውበት ለጥበብ አፍቃሪያኑ አስተዋውቀዋል።
ሠዓሊ እያሱ ሲሳይ፤ በተሰጠኝን መክሊ የተለያዩ ስዕሎችን በማዘጋጀት አገሬን በዓለም መድረክ ለማስተዋወቅ ችያለሁ ሲል ይገልጻል።
“ሥዕልን የምስለው የነበሩ ታሪኮቻችንን፣ ውበት፣ ባህል፣ ቋንቋ፣ የሀገር ገፅታ መልከዓ-ምድር ውበት እና ሳቢነትን በመጨመር ሰዎች ሲያዩት መንፈሳቸው የሚታደስበት ሁኔታ ለመፍጠር ነው” ይላል።
በተጨማሪም ለትውልድ የሚተላለፉ ታሪኮችን ለማስተዋወቅ ስዕልን እንደሚያዘወትር ይናገራል።
ከተወሰኑ ዓመታት ወዲህ የሥዕል ሥራዎቹ ላይ ቡናማ ቀለምን በብዛት አካቶ እንደሚሰራ የተናገረው ሠዓሊው፤ ይህም የቡና መገኛ የሆነችው ኢትዮጵያን ለማስተዋወቅ ምክንያት እንደሆነው ይናገራል።
የሥዕል ሥራዎቹን በሀገር ውስጥ እና ከሀገር ውጭ በተለያዩ የአውሮፓ እና ዓለም አቀፍ የስዕል ኤግዚቢሽኖች ላይ ያቀረበ ሲሆን፤ በየመድረኮቹ ላይ የሀገሩን ባህል እና ወግ እንዲሁም ታሪክ ማሳየቱን ነው የሚያስረዳው።
ሠዓሊው በቀጣይ ሥራዎቹን ለሕዝብ ለማድረስ ዝግጅት እያደረገ እንደሆነ እና በተለይ ቡና ተኮር የሆኑ የሥዕል ስራዎቹን ከታሪክ ጋር በማስተሳሰር በቀጣይ ኤግዚቢሽኖች ላይ ለማቅረብ ውጥን እንዳለው ተናግሯል።
