የትግራይ የጤና ባለሙያዎች የ17 ወራት ውዝፍ ደመወዝ እንዲከፈላቸው በሰልፍ ጠየቁ
የትግራይ ክልል የጤና ባለሙያዎች በክልሉ በተካሄደው ጦርነት ወቅት ሳያገኙ የቀሩት የ17 ወራት ውዝፍ ደመወዝ እንዲከፈላቸው በሰልፍ ጠየቁ። የጤና ባለሙያዎቹ ምቹ የስራ ሁኔታ እንዲፈጠርላቸውም ጥያቄ አቅርበዋል።
ባለሙያዎቹ ጥያቄያቸውን ያሰሙት፤ ትላንት ረቡዕ ሚያዝያ 29፤ 2017 ዓ.ም. በመቐለ ከተማ በሚገኙ የተለያዩ የጤና ተቋማት ውስጥ ባካሄዱት ሰላማዊ ሰልፍ ነው። ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ተከታታይ ቀናት በክልሉ በሚገኙ የተለያዩ የጤና ተቋማት እንደሚካሄድ የተገለጸውን ይህ ሰላማዊ ሰልፍ የጠራው የትግራይ የጤና ባለሙያዎች ማህበር ነው።
የማህበሩ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ፍስሃ አሸብር የጤና ባለሙያዎች በትግራይ ጦርነት ወቅት በስራ ገበታቸው በመገኘት ለህዝብ አገልግሎት ሲሰጡ መቆየታቸውን አስታውሰዋል። የጤና ባለሙያዎቹ የህክምና አገልግሎት ሲሰጡ የቆዩት፤ ለ17 ወራት ያህል ደመወዝ ሳይከፈላቸው እንደነበርም ጠቁመዋል።
