ለስድስት ዓመታት ተቋርጦ የነበረው የቻይና እና የሰሜን ኮሪያ የባቡር ትራንስፖርት ዳግመኛ መጀመሩን ተከትሎ በሁለቱ አገራት መካከል ያለው ግንኙነት አዲስ ምዕራፍ መያዙ ተነገረ።
በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ተቋርጦ የነበረው ይህ የባቡር መስመር፣ ከነገ ጀምሮ በሳምንት ለአራት ቀናት ከቤጂንግ ወደ ፒዮንግያንግ መደበኛ ጉዞውን እንደሚጀምር የቻይና ባቡር ባለሥልጣን አስታውቋል።
ምንም እንኳ ቻይና ከወረርሽኙ ማግስት በፍጥነት ወደ መደበኛ እንቅስቃሴ ብትመለስም፣ ሰሜን ኮሪያ ጥብቅ የድንበር ገደቦችን ለማላላት ረጅም ጊዜ ወስዶባታል።
በአሁኑ ወቅት ጉዞው የተፈቀደላቸው ቪዛ ያላቸው ጥቂት የውጭ አገር ዜጎች፣ በሰሜን ኮሪያ የሚኖሩ ወይም የሚማሩ ቻይናውያን ብቻ መሆናቸው ተገልጿል።
የጉዞ ወኪሎች ለነጋዴዎችና ለቱሪስቶች የሚሆን በቂ ትኬት እስካሁን ይፋ እንዳልተደረገ ቢጠቁሙም፣ የትራንስፖርት አገልግሎቱ መጀመር የሁለቱን አገራት ዲፕሎማሲያዊና ኢኮኖሚያዊ ወዳጅነት ይበልጥ እንደሚያጠናክረው ይጠበቃል።
