ኢትዮጵያ እያደገ የመጣውን የኃይል ፍላጎት ለማሟላት እና የኢኮኖሚ ተግዳሮቶቿን ለመቅረፍ የኒውክሌር ኢነርጂን ለሰላማዊ ልማት ለመጠቀም ቁርጠኛ አቋም መያዟን አስታወቀች።
በፈረንሳይ ፓሪስ በተካሄደው ሁለተኛው የኒውክሌር ኢነርጂ ጉባኤ ላይ ንግግር ያደረጉት የመስኖ እና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር አብርሃም በላይ፤ ሀገሪቱ ከአቶሚክ ኢነርጂ የምትፈልገው “ኪሎዋት እንጂ የጥይት አረር አይደለም” በማለት የሰላማዊ አጠቃቀም ፍላጎቷን በግልጽ አስምረውበታል።
ኢትዮጵያ እስካሁን በታዳሽ ኃይል ላይ ብትመሰረትም፣ የነባር የኃይል ምንጮች አቅርቦት ከፍላጎቱ ጋር ሊመጣጠን አለመቻሉ ለዚህ ሉዓላዊ ውሳኔ መነሻ ሆኗል።
ሀገሪቱ ከሩሲያው ሮሳቶም ጋር የጀመረችው ስምምነትና በዓለም አቀፉ የኒውክሌር ኤጀንሲ መሪነት የሚከናወነው ኃላፊነት የተሞላበት አስተዳደር፣ ኢትዮጵያ የኒውክሌር ቴክኖሎጂን ለህዝቦቿ ብልጽግና ለማዋል የያዘችውን ስልታዊ እቅድ የሚያጠናክር ነው።
ይህ እርምጃ ኢትዮጵያን በኃይል አቅርቦት ራሷን የቻለችና በቴክኖሎጂ የላቀች ሀገር ለማድረግ በሚደረገው ጉዞ ውስጥ ወሳኝ ምዕራፍ ተደርጎ ይወሰዳል።
