የአሜሪካ ሕግ አውጪዎች ሶማሊላንድ ለዓመታት የቆየባትን የፋይናንስ ማግለል በመስበር በቀጥታ ከዓለም አቀፉ ኢኮኖሚ ጋር እንድትገናኝ የሚያስችል አዲስ ረቂቅ ሕግ ለኮንግረሱ አቅርበዋል።
ይህ እርምጃ ዋሽንግተን ለአፍሪካ ቀንድ ያላትን የጂኦፖለቲካዊ ፖሊሲ የቀየረ ትልቅ ክስተት ተደርጎ የተወሰደ ሲሆን፣ ረቂቅ ሕጉ ከ6 ሚሊዮን በላይ ለሚሆነው የሶማሊላንድ ሕዝብ የSWIFT የባንክ አገልግሎት ተደራሽነትን ጨምሮ ሀገሪቱ ከዓለም አቀፍ የባንክ መሠረተ ልማት ጋር እንድትተሳሰር የሚያስችሉ ግልጽ የሆኑ የፖሊሲ አቅጣጫዎችን ያስቀምጣል።
በተጨማሪም የአሜሪካ የግምጃ ቤት ሚኒስቴር በ180 ቀናት ውስጥ ኃላፊነት የተሞላበት የአሜሪካ ኢንቨስትመንት በሶማሊላንድ የሚስፋፋበትን ስትራቴጂ እንዲያዘጋጅ የሚያዝዝ ሲሆን፣ በሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር እና በሽብርተኝነት ላይ የሚደረገውን የሁለትዮሽ ትብብር ለማጠናከር ያለመ መሆኑ ተጠቁሟል።
ረቂቅ ሕጉ ከጸደቀ ለውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት መከፈት፣ የንግድ መስመሮች መስፋፋት እና ሶማሊላንድ በቀጣናው ቁልፍ የኢኮኖሚ መተላለፊያ ሆና እንድትወጣ ትልቅ ዕድል ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል።
