በኢትዮጵያ የሚዲያ ዘርፍ አዲስ ምዕራፍ የከፈቱት እና የኢቢኤስ ቴሌቪዥን መሥራች እና ዋና ሥራ አስፈጻሚ የነበሩት የአቶ አማን ፍስሐ ጽዮን የቀብር ሥነ-ሥርዓት ሐሙስ የካቲት 12 2018 ዓ .ም ተፈጽሟል።
ቀደም ሲል በዓድዋ ድል መታሰቢያ በተከናወነው የክብር ሽኝት መርሐ-ግብር ላይ የቤተሰብ አባላት የአቶ አማንን መልካም አባትነት እና ለቤተሰባቸው የነበራቸውን ጥልቅ ፍቅር የሚዘክሩ ልብ የሚነኩ ንግግሮችን አድርገዋል።
የሃይማኖት አባቶች አቶ አማን በኢቢኤስ ቴሌቪዥን ሁሉም እምነቶች በእኩልነት ለተከታዮቻቸው አስተምህሮታቸውን መንገድ የከፈተ ሚዲያ እንዲሆን ማስቻላቸውን መስክረዋል።
በተለይም በኮቪድ 19 ወቅት ከእምነት ተቋማት ጋር የሠሩት ሥራ ሲያስመሰግናቸው እንደሚኖር ነው የገለጹት።
ባለትዳር እና የሦስት ልጆች አባት የነበሩት አቶ አማን ፍስሐ ጽዮን ከቤተሰብ ኃላፊነታቸው ባሻገር፣ በሚሊዮኖች ዘንድ ተወዳጅ የሆነውን ኢቢኤስን በመመሥረት ለሀገራቸው ተወዳጅ የሚዲያ ውጤት ያበረከቱ ታታሪ መሪ እንደነበሩ ይመሰከርላቸዋል።
የአቶ አማን ፍስሐ ጽዮን ሥርዓተ ቀብር በአዲስ አበባ የቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ መካነ መቃብር ወዳጅ ዘመዶቻቸው፣ የሥራ ባልደረቦቻቸው እና በርካታ የጥበብ ሰዎች በተገኙበት ተፈጽሟል።
