የአፍሪካ ልማት ባንክ ለዳሸን ባንክ የ40 ሚሊዮን ዶላር የንግድ ፋይናንስ ዋስትና ብድር እንዳፀደቀ ዛሬ ሚያዝያ 22 ቀን 2017 ዓ.ም በዳሸን ባንክ ዋና መሳሪያ ቤት በተከናወነ ሥነሥርዓት ይፋ ተደርጓል።
አህጉራዊው የልማት ባንክ ያደረገው የዋስትና ብድር የኢትዮጵያን የፋይናንስ ዘርፍን ለማጠናከር፣ አነስተኛ፣ መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችን እና የሀገር ውስጥ ኮርፖሬሽኖችን ለመደገፍ ያለመ ነው ተብሏል።
የተፈቀደው የፋይናንስ ዋስትና ብድር የኢትዮጵያን የግብርና እና የማኑፋክቸሪንግ ዘርፎችን ለማነቃቃት ወሳኝ የሆኑትን እንደ ማዳበሪያ፣ ፋርማሲዩቲካል፣ የፀሐይኃይል ፓነሎች እና የእርሻ ማሽነሪዎችን ጨምሮ ሌሎች አስፈላጊ ዕቃዎችን ወደ ሀገር ውስጥ ለማስገባት ድጋፍ ያደርጋልም ተብሏል።
ዳሸን ባንክ ያገኘው ድጋፍ የገቢ እና የወጪ ንግድ ፋይናንስ መስፈርቶችን እንዲያሳልጥ በማድረግ ባንኩ የኢትዮጵያ ወሳኝ የኢኮኖሚ ዘርፎች ለመደገፍ ያለውን አቅም የሚያሳድግ እንደሆነም ተነግሯል።
በዚህ የንግድ ፋይናንስ ዋስትና ብድር መሰረት የአፍሪካ ልማት ባንክ በዳሸን ባንክ ለሚቀርቡ ክፍያ ላልተከፈለባቸው ከንግድና ፋይናንስ ጋር ለተገናኙ ሰነዶች የባንክ ፍቃድ ዋስትና እንደሚሰጥም ተገልጿል።
