የኢትዮጵያ የልብ ሕሙማን ሕጻናት መርጃ ማዕከል በመድኃኒቶችና በአላቂ እቃዎች እጥረት ምክንያት መስጠት ከሚገባው በ3 እጥፍ ያነሰ አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝ የማዕከሉ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ህሩይ አሊ ለአሐዱ ተናግረዋል፡፡
ኢትዮጵያ ካላት የሕዝብ ቁጥር አንፃር ከሚያስፈልጋት የልብ ሕክምና መስጫዎች ወስጥ በሕጻናት ዘርፍ ብቸኛው ማዕከል መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፤ ነገር ግን በአቅሙ ልክ እየሰራ እንዳልሆነ ተጠቁሟል።
የማዕከሉ ዋና ሥራ አስፈፃሚ “በኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት የሚቀርቡ መድኃኒቶች ቢኖሩም፤ ከሚያስፈልገን አንፃር በቂ አይደለም” ብለዋል።
“በሁሉም በኩል መነሳሳቶች አሉ ነገር ግን አሁንም ችግሮቹ አልተፈቱም አቅማችንንም ሙሉ በሙሉ መጠቀም አልቻልንም” ሲሉም ተናግረዋል።
የልብ ሕሙማን ሕጻናት መርጃ ማዕከሉ ከዩኒቨርሲቲ ሆስፒታሎች ከጥቁር አንበሳ ሆስፒታል እና ከጳውሎስ ሆስፒታል ጋር በጋራ ሥራዎች እየተሰራ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል፡፡
“ነገር ግን አሁንም ወረፋ የሚጠብቁ እና በየቀኑ ለሕክምና የሚመጡ ታካሚዎች ቁጥር ከፍተኛ ነው” ብለዋል አቶ ህሩይ አሊ።
ከዚህ በፊት በተደረገ ጥናት ኢትዮጵያ 24 የልብ ሕክምና መስጫዎች ቢያስፈልጓትም፤ ግማሹን እንኳን ማሟላት እንዳልተቻለ ነው የተገለጸው።
በተለይ በሕጻናት የልብ ቀዶ ሕክምና ማዕከልነት ብቸኛው የሆነው ማዕከልም 80 ከመቶ የሚሆኑትን መድኃኒቶች ከውጭ የሚያስገባ በመሆኑ እና ውድ በመሆናቸው በአቅሙ ልክ መስራት እንዳልቻለ ተመላክቷል።
በዚህም ማህበረሰቡም መከላከሉ ላይ ማተኮር አለበት የተባለ ሲሆን፤ ሕጻናት በተደጋጋሚ ቶንሲል የሚከሰትባቸው ከሆነ በቶሎ ወደ ሕክምና በመሄድ መመርመር አለባቸው ተብሏል፡፡ እንደ ትምህርት ቤት ያሉ ተቋማትም ሕብረተሰቡን ማስተማር ላይ ማተኮር እንዳለባቸው ተገልጿል።
(አሐዱ ሬድዮ)
