የኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳይያስ አፈወርቂ የሳዑዲ ዓረቢያ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከሆኑት ዋሊድ ቢን አብዱልከሪም አልኬሬጂ ጋር በአስመራ ተገናኝተው ውይይት ማካሄዳቸውን የኤርትራ የማስታወቂያ ሚኒስቴር አስታወቀ።
ሐሙስ ዕለት በደንደን የእንግዳ ማረፊያ በተካሄደው በዚህ ስብሰባ ላይ፣ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን የቆየ የሁለትዮሽ ግንኙነት ማጠናከር እንዲሁም በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ፣ በደህንነት፣ በባህልና በማህበራዊ ዘርፎች ትብብርን ማስፋፋት በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ትኩረት መደረጉን ሚኒስቴሩ ገልጿል።
ሚኒስቴሩ እንዳስታወቀው፣ ውይይቱ ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ክስተቶችን የተመለከቱ የጋራ እሳቤዎችን ያካተተ ሲሆን፤ በተለይም የቀይ ባሕር ዳርቻ አገራት ለቀጣናዊ ሰላምና መረጋጋት ሊኖራቸው በሚገባው ሚና ላይ ትኩረት ሰጥቷል።
በውይይቱ ላይ የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኡስማን ሳሌህ የተገኙ ሲሆን፣ ከሳኡዲ ወገን ደግሞ በአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዋና ዳይሬክተር አምባሳደር ሳቅር ቢን ሱሌይማን አል-ቁራሺ እና በኤርትራ የሳኡዲ አምባሳደር መሻል ሀምዳን አልሮጊን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የሳዑዲ ባለስልጣናት ተሳትፈዋል።
ይህ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በአስመራ እና በባህረ ሰላጤው አገራት መካከል ከፍተኛ እንቅስቃሴ በሚታይበት ወቅት የተከናወነ ሲሆን፤ ይህም የአፍሪካ ቀንድን ከባህረ ሰላጤው ቀጣና ጋር በሚያገናኘው የቀይ ባሕር መስመር ላይ እያደገ የመጣውን ጂኦፖለቲካዊ ፍላጎት የሚያንጸባርቅ ነው ተብሏል።
በጎርጎሮሳውያኑ ታህሳስ 2025፣ የሳኡዲ ዓረቢያው አልጋ ወራሽ መሐመድ ቢን ሰልማን ፕሬዝዳንት ኢሳይያስን በሪያድ ተቀብለው ያነጋገሩ ሲሆን፤ በወቅቱም ሁለቱ መሪዎች የሁለትዮሽ ትብብርን ማስፋፋት በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ መምከራቸው የሚታወስ ነው።
ይህ ውይይት በቅርቡ የሳዑዲ ዓረቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ልዑል ፋይሰል ቢን ፋርሃን ቢን አብዱላህ በአዲስ አበባ ያደረጉትን ጉብኝት ተከትሎ የመጣ ሲሆን፤ ሚኒስትሩ በወቅቱ ከኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጋር በሁለትዮሽ ግንኙነት፣ በቀጣናዊ ደህንነት እና ከስደት ጋር በተያያዙ የትብብር ጉዳዮች ላይ መወያየታቸው ይታወሳል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ውይይቱ ዘመን ተሻጋሪ የሆነውን ግንኙነት ማጠናከር፣ ቁልፍ በሆኑ ዘርፎች ላይ ትብብርን ማስፋፋት እንዲሁም በቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ላይ ቅንጅትን ማሳደግ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ መሆኑን ገልጸዋል።
