የ ” ማንኛችን በነውር እንበልጣለን ? ” ፉክክር

Date:


         ትናንት የአርቲስት ደበበ እሸቱ የቀብር ስርዓት በአመዛኙ የመንግሥት ሰዎች በተገኙበት ተከናውኗል ። እንደ አርቲስቱ ታላቅነት ፣ እንደ አንጋፋነቱ ፣ ለኪነጥበቡ እንዳበረከተው አስተዋጽዖ የሚጠበቀውን ያህል ሰው በሽኝቱ ላይ አልተገኘም ።

አጋጣሚ ሆኖ የዛሬ 13 ዓመት ልክ በትናንቱ ዕለት የአቶ መለስ ሕልፈት ( በእርግጥ ቀኑ አወዛጋቢ ነው ) የተነገረበት ነው ። ሁለቱን ሰዎች ጎን ለጎን ያመጣኋቸው የሁለቱን ሕልፈት አስመልክቶ ስለተነከሰቱ አፈንጋጮች ( በባሕልና በስነምግባር ) ለማለት ነው ።

አቶ መለስ የሞቱ ጊዜ ከዲያስፖራዎች ጥቂት ተቃዋሚዎች በሞንታርቦ ሙዚቃ ከፍተውና ባንዲራ ለብሰው አደባባይ ላይ ሲጨፍሩ አቶ መለስን በሚቃወሟቸውና በሚጠሏቸው ጭምር ተወግዘዋል ። ምክንያቱም ነውሩ ከኢትዮጵያዊ ስነምግባር ያፈነገጠ በመሆኑ ።

በወቅቱ እንደ አጠቃላይ ሀገሬው ፣ ይበልጥ ደግሞ ተጋሩው ሀዘን ተሰምቷቸዋል ። ስሜታቸው ተጎድቷል ። ጉዳዩን ከብሔር መገለል ጋር ያያያዙትም ነበሩ ። በወቅቱ በድርጊቱ ያላዘነና ክፉ ያልተሰማው ተጋሩ ነበረ ብዬ አላምንም ።

       ከእነዚያ ሰዎች ጥቂት የማይባሉት የአርቲስት ደበበ እሸቱ ሕልፈት ከተሰማ ዕለት አንስቶ ከበሮ እየደለቁ ይገኛሉ ። አስከሬን ሲሰድቡና ሲያንጓጥጡ ነው ውለው ያደሩት ። ትናንት በአስከሬን ሽኝቱም ሆነ ስርዓተ ቀብሩ ላይ ብዙ ሕዝብ አለመገኘቱ አንድ የተቃውሞ መንገድ አድርጌ እወስደዋለሁ ።

የሰዉ ሁሉ መብት ነው ። ማንም ሊከሰው አይችልም ። ራሱ ጋሽ ደበበ በሕይወት እያለ ” ብልጽግናን ትደግፋለህ ” ሲባል ” ደግ አደረግሁ ። እኔ ብልጽግናን ሳይሆን ዶ/ር ዐቢይን ነው የደገፍኩት ። ለእሱ ደግሞ ደግ አደረግሁ ” ብሏል ። ምርጫ ነው ። በግሌ ” ሙት አይወቀስም ” ከሚሉት መሐል አይደለሁም ።

ሰው ሲሞት በሕይወት እያለ በሰራው መልካም ተግባር እንደምናመሰግነው ባልተገባ ስራው ብንወቅሰው ነውር አይመስለኝም ። ወይም ነው ብዬ አላምንም ። ሰው መልካምም ቢሰራ ፣ ቢከፋም ለሌላው ነው ። ለራሱ ምንም አይደለም ። ሰው የመልካምና የክፉ አርአያ ነው ።

       ሰው ከሞተ በኋላ በስራው ሲወቀስ ወደፊት በትንሳኤ ሲነሳ እንዲያስተካክለው አይደለም ። ሌሎች የተባለውን አይተው ” ነግ በእኔ ” እንዲሉ ነው ። አስከሬንን መስደብና ማንጓጠጥ ግን በምንም መመዘኛ ኢ – ሞራላዊ ነው ። በዚያን ወቅትም ” አቶ መለስን ኢትዮጵያ ላይ ባላቸው አቋም በግሌ ተቀዋሚያቸው ነኝ ።

ሆኖም ግን አሁን በሀገር ባሕል መሰረት ግብዐተ መሬታቸው ሳይፈጸም አንወቅሳቸውም ” እያሉ በጨዋ ደንብ አስተያየት የሰጡ ብዙ ናቸው ። የአቶ መለስ ሕልፈት ጊዜ ጥቂት ዲያስፖራዎች ያደረጉት ዛሬም ድረስ በነውርነቱ ተመዝግቦ ተቀምጧል ። ይህ ከሆነ ደግሞ በደበበ እሸቱ ላይ የተደረገውም ስህተት ነው ።

መርጦ ልክ መሆን የለም መቸም ። የጋሽ ደበበን የቀደመ ሀሳብና ስራ ( ለምሳሌ ከብልጽግና ጎን መቆሙንና ጠቅላይ ሚኒስትሩን መደገፉን ) መቃወም ችግር የለውም ። መጥላትም ጠዪው በዚህ ይጠቀም ከሆነ ችግር የለውም ። በጋሽ ደበበ ሽኝትና ቀብር ላይ የሚጠበቀውን ያህል ሰው በሽኝቱ ላይ አለመገኘቱን ” ለምን ? ” የሚል የለም ።

የየባለቤቱ መብት ነው ። መንግሥትም በራሱ መንገድ ዘመኑን በአርቲስትነት ያሳለፈውን ደበበን በባለስልጣን ማዕረግ አስቀብሮታል ። አስከሬንን መሳደብና ማንቋሸሽ ግን የ ” ማንኛችን በነውር እንበልጣለን ? ” እንጂ ሌላ ምን ይሆናል ?

ከቴዎድሮስ ተ/አረጋይ

ያጋሩ!

መጽሔቶች

በብዛት የተነበቡ

ተጨማሪ ጽሑፎች
ተመሳሳይ

✌️ጀግናን ማክበርና መሸለም ጀግንነት ነው

✌️ከዕድሜው የገዘፈው የታሪኩ ጁዋር ጀግናውን ሙሉጌታ ከበደን የመዘከር የጀግንነት...

የአህጉሪቱን የርስ በርስ ንግድ ልውውጥ 250 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ታቀደ

የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጠና ዋና ፀሐፊ ዋምኬሌ ሜኔ...

በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፉ መርከቦች ክፍያ መፈጸም አይጠበቅባቸውም

አሜሪካ እና ኢራን በተስማሙበት የመግባቢያ ሰነድ መሠረት በሆርሙዝ ወሽመጥ...

እስራኤል ጦሯ በደቡብ ሊባኖስ እንደሚቆይ አስታወቀች

የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እስራኤል ካትዝ እንደተናገሩት፤ በአሜሪካ እና በኢራን...