በአዲስ አበባ ከተማ በብዛት የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡት “ሚኒባስ” ታክሲዎች ያለ ረዳት መንቀሰቀሳቸው ሕገ-ወጥ እንደሆነ እና ደንቡን ተላልፈው በተገኙ አሽከርካሪዎች ላይ የቅጣት እርምጃ እንደሚወሰድ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አስታውቋል።
በከተማዋ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ያለረዳት የሚያሽከረክሩ የከተማ ታክሲዎችን ቁጥር መጨመር አስመልክቶ አሐዱ ያነጋገራቸው ተሳፋሪዎች ባሰሙት ቅሬታ፤ “አሽከርካሪዎች እያሽከረከሩ አገልግሎት የሰጡበትን ሒሳብ በሚቀበሉበት ጊዜ አደጋ ሊያደርሱ የሚችሉበት ዕድል ከፍተኛ በመሆኑ ሊታሰብበት ይገባል” ብለዋል።
“ማሽከርከር ሙሉ ትኩረትን የሚፈልግ ነው!” ያሉት አስተያየት ሰጪዎቹ፤ “አሽከርካሪዎቹ የረዳትን ሥራ ደርበው ለመስራት በሚያደርጉት ጥረት ከፍተኛ ስጋት የሚፈጥር በመሆኑ ሊታረም ይገባል” ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል።
በኮሚሽኑ የትራፊክ አደጋ ምርመራ የግድያና አደጋዎች መርማሪ ኢንስፔክተር ተመስገን ደሳለኝ “የከተማ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ አሽከርካሪዎች ያለ ረዳት ማሽከርከራቸው በሕግ የተከለከለ ነው” ብለዋል።
“መሰል ድርጊቶች ለመንገድ ላይ አደጋዎች መፈጠር ከፍተኛ አስተዋጽኦ አላቸው” ያሉት ኢንስፔተክተር ተመስገን፤ አሽከርካሪዎች ሙሉ ትኩረታቸውን በማሽከርከር ሥራቸው ላይ አለማድረጋቸው የመንገድ ላይ ክስተቶችን ለመቆጣጠር እንዳይችሉ እና አደጋ እንዲፈጠር የሚያደርግ በመሆኑ የተከለከለ መሆኑን ተናግረዋል።
“ይህንን ደምብ ተላልፈው በተገኙ አሽከርካሪዎች ላይም ቅጣት ይጣላል” ሲሉ አሳስበዋል።
መርማሪው፤ አሽከርካሪዎች የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ ከመሰል ድርጊት መቆጠብ እንዳለባቸው በማሳሰብ፤ ነዋሪዎችም መሰል የደንብ ጥሰቶች በሚያጋጥሙበት ወቅት ለቁጥጥር ባለሞያዎች ጥቆማ በመሰጠት እንዲተባበሩ ጥሪ አቅርበዋል።
