የእስራኤል ኃይሎች በጋዛ ሰርጥ ባደረሱት ተከታታይ ጥቃቶች ቢያንስ 95 ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ።
ጥቃቱ በጋዛ ሰርጥ በሚገኝ አንድ ካፌ፣ ትምህርት ቤት እና የምግብ ማከፋፈያ ጣቢያዎች ላይ የተሰነዘሩ ሲሆን ቢያንስ 95 ሰዎች መሞታቸው ነው የተገለጸው ።
በተፈጸሙት ጥቃቶች ከተጎጂዎች መካከል ቢያንስ 62 የሚሆኑት በጋዛ ከተማ እና በግዛቱ ሰሜናዊ ክፍል የሚገኙ ናቸው።
በተለይ በሰሜናዊ ጋዛ በሚገኘው አል-ባቃ ካፌ በተባለ የባህር ዳርቻ ምግብ ቤት ላይ የተፈጸመው የአየር ጥቃት ከፍተኛ ጉዳት አስከትሏል። ጥቃቱን ተከትሎ የወጡ ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት፣ በዚህ ካፌ ብቻ 39 ሰዎች ሲሞቱ፣ በርካቶች ቆስለዋል።
በዚህ አሰቃቂ ክስተት ህይወታቸውን ካጡት መካከል እስማኤል አቡ ሃታብ የተባለ ጋዜጠኛ ይገኝበታል። በአል-ባቃ ካፌ ውስጥ ተሰብስበው የነበሩ በርካታ ሴቶችና ህጻናትም በጥቃቱ ህይወታቸውን አጥተዋል።
የዓይን እማኞች እንደገለጹት፣ የእስራኤል ተዋጊ ጄቶች በጥቃቱ መሳተፋቸውን ተናግረዋል ሲል አልጄዝራ ዘግቧል ።
