ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ከኩዌቱ አልጋ ወራሽ ጋር በዛሬ ዕሁድ በስልክ ባደረጉት ውይይት፣ በኢራን የተፈጸመውን ጥቃት በጽኑ መኮነናቸውንና ኢትዮጵያ ከኩዌት ጎን መቆሟን መግለጻቸውን የኩዌት የዜና አገልግሎት (ኩና) ዘግቧል።
እንደ ዘገባው ከሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከልዑል አልጋ ወራሽ ሼክ ሳባህ ካሊድ አል-ሐማድ አል-ሳባህ ጋር ባደረጉት የስልክ ውይይት፣ የኩዌትን ሉዓላዊነት፣ የአየር ክልል፣ ዓለም አቀፍ ሕግጋትን እና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ቻርተርን የጣሰ ነው ያሉትን ጥቃት አውግዘዋል።
በውይይቱ ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ኢትዮጵያ የኩዌትን የሲቪል ተቋማት ኢላማ ያደረገ ማንኛውንም ጥቃት እንደማትቀበል በግልጽ አስምረውበታል ተብሏል።
በተጨማሪም ኩዌት ሉዓላዊነቷን፣ መረጋጋቷን እና ደህንነቷን ለመጠበቅ ለምትወስደው ማንኛውም እርምጃ ኢትዮጵያ ለሀገሪቱ አመራሮች፣ መንግሥት እና ሕዝብ ያላትን ጽኑ ድጋፍ አረጋግጠዋል።
ይህ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የተደረገው፣ ኢራን በባሕረ ሰላጤው ሀገራት ላይ የሰነዘረችውን የሚሳኤል እና የድሮን ጥቃት ተከትሎ ቀጣናዊ ውጥረት በነገሰበት ወቅት ነው።
እንደ ኩና ዘገባ፣ አልጋ ወራሹ የኩዌቱ አሚር ሼክ መሻል አል-አሕመድ አል-ጃቢር አል-ሳባህ ለኢትዮጵያው ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ ሰላምታ በማስተላለፍ ኢትዮጵያ ለኩዌት ላሳየችው ጽኑ ድጋፍ ያላቸውን ጥልቅ አድናቆት ገልጸዋል። አልጋ ወራሹ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይም “ልባዊ እና ወንድማማቻዊ” ላላቸው ቅድሚያ ተነሳሽነት ምስጋና አቅርበዋል።
