የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ላይ በተከፈተው ጦርነት ያቀድናቸውን “ግቦች ለማሳካት እጅግ በመቃረባችን” ጦርነቱን “ለማጠቃለል እያሰብን ነው” ሲሉ ተናገሩ።
ኢራን የዘጋችውን የሆርሙዝ ወሽመጥ የማስከፍት ጉዳይ ግን የመርከብ መተላለፊያ መስመሩን “የሚጠቀሙት አገራት” ኃላፊነት መሆን እንዳለበት ገልጸዋል።
ትራምፕ ‘ትሩዝ ሶሻል’ በተባለው የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ፤ “ግቦቻችንን ለማሳካት በጣም እየተቃረብን በመሆኑ፤ ሽብርተኛውን የኢራን አገዛዝ በተመለከተ፤ በመካከለኛው ምሥራቅ የምናደርገውን ታላቅ ወታደራዊ ጥረት ለማቆም እያሰብን ነው” ብለዋል።
እንደ ፕሬዝዳንቱ ገለጻ ኢራን ላይ የተከፈተው ጥቃት አምስት ዓላማዎች ነበሩ። በቀዳሚነት የጠቀሱት “የኢራንን ሚሳዔል አቅም፣ ማስወንጨፊያዎች እና ተያያዥነት ያላቸው ነገሮችን በጠቅላላ ሙሉ በሙሉ ማዳከም” የሚለውን ነው።
“የኢራንን የመከላከያ ኢንዱስትሪ ሰፈርን ማውደም” እንዲሁም የአገሪቱን “የባሕር እና የአየር ኃይል፣ የፀረ-አውሮፕላን የጦር መሣሪያዎችን ጭምር ማጥፋት” የሚለውን ከግቦቹ መካከል ጠቅሰዋል።
ትራምፕ በአራተኛነት የጠቀሱት ግብ “ኢራን ፈጽሞ ወደ ኒውክሌር አቅም እንዳትቀርብ ማድረግ” እና አድርጋ ከተገኘችም አሜሪካ “በፍጥነት እና በኃይል ምላሽ መስጠት የምትችልበት ደረጃ” ላይ እንድትሆን ማድረግን ነው።
እንዲሁም እስራኤል፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ ኳታር፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፣ ባህሬን፣ ኩዌት እና ሌሎችንም የመካከለኛው ምሥራቅ የአሜሪካ አጋሮችን “በከፍተኛ ደረጃ መጠበቅ” ከግቦቹ አንዱ መሆኑን ገልጸዋል።
ፕሬዝዳንቱ በዚህ ልጥፋቸው የተለያዩ አገራትን እገዛ ጠይቀው በጎ ምላሽ ስላላገኙበት የሆርሙዝ ወሽመጥ ጉዳይም አንስተዋል።
“እንደ አስፈላጊነቱ የሆርሙዝ ወሽመጥ በሚጠቀሙበት ሌሎች አገራት ሊጠበቅ እና ቁጥጥር ሊደረግበት ይገባል፤ አሜሪካ ግን አትጠቀምበትም!” ሲሉ የባሕር መስመሩን ማስከፈት የአገራቸው ኃላፊነት እንዳልሆነ አመልክተዋል።
ይሁን እንጂ ወሽመጡን የሚጠቀሙበት አገራት የአሜሪካንን እገዛ ፈልገው ጥያቄ የሚያቀርቡ ከሆነ ግን “እናግዛቸዋለን” ብለዋል።
“ነገር ግን አንዴ የኢራን ስጋት ከተወገደ በኋላ ግን [የሆስሙዝ ወሽመጥን መጠበቅ] አስፈላጊ አይሆንም። ቀላል ወታደራዊ ዘመቻ ይሆንላቸዋል” ሲሉ ጽፈዋል።
BBC
