በፖሊስ በተወሰዱት የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎች ውስጥ የሚገኙ ከስራ ጋር የተያያዙ እና የግል መረጃዎች አላግባብ ጥቅም ላይ ሊውሉ ይችላሉ ሲል ስጋቱንም ገልጿል
ፖሊስ በአዲስ ስታንዳርድ ላይ ባደረገው ብርበራ በወሰዳቸው የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎች ውስጥ የሚገኙ ከስራ ጋር የተያያዙ እና የግል መረጃዎች አላግባብ ጥቅም ላይ ሊውሉ ይችላሉ ሲል የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች የሆነው ተቋም (ሲፒጄ) ትላንት ሚያዚያ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ ስጋቱን አስታወቀ።
በአዲስ ስታንዳርድ ላይ ፖሊስ እያካሄደ ያለውን ምርመራ እንዲያቋርጥ የጠየቀው ሲፒጄ፤ የተወሰዱት የተቋሙ የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችንም በአፋጣኝ እንዲመልስ አሳስቧል።
“አዲስ ስታንዳርድ ላይ የተፈጸመው ብርበራ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የኢትዮጵያ መንግስት ነፃ ሚዲያዎችን ዝም ለማሰኘት እያካሄደው ያለው ዘመቻ አካል ነው፤ የተቋሙን የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎች መውሰዱ በውስጣቸው የሚገኙ ከስራ ጋር የተያያዙና የግል መረጃዎች አላግባብ ጥቅም ላይ ሊውሉ የሚችልበት እድል ከፍተኛ ነው” ሲሉ የሲፒጄ አፍሪካ ፕሮግራም አስተባባሪ ሙቶኪ ሙሞ ስጋታቸውን መግለጻቸውን አስታውቋል።
ስድስት የደንብ ልብስ ያልለበሱ የፖሊስ አባላት መሆናቸውን የገለጹ ሰዎች ሚያዝያ 9 ቀን2017 ዓ.ም የአዲስ ስታንዳርድን ቢሮ መበርበራቸውን፣ የዜና ክፍል ኃላፊውንና የሰው ሃብት አስተዳደር ሃላፊውን ለምርመራ ወደ ፌደራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ቢሮ መውሰዳቸውን የድርጅቱ መስራች ፀዳለ ለማ ለጋዜጠኞች መብት ተሟጋቹ ተቋሙ (CPJ) ተናግረዋል።
ፖሊሶቹ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ እንዳላቸው ቢናገሩም፣ ግልባጭ ሳያሳዩ ወደ ተቋሙ ቢሮ ዘው ብለው መግባታቸውን፤ የተቋሙ ጋዜጠኞች ሁከት ሊያስከትል የሚችል ዘጋቢ ፊልም በማዘጋጀት ተጠርጥረው ምርመራ እየተደረገባቸው እንደሆነ እንደነገሯቸው ፀዳለ ተናግረዋል፡፡
አክለውም፤ ክሱ ሀሰት መሆኑንና ድርጅቱ ዘጋቢ ፊልሞችን የማዘጋጀት አቅም እንደሌለው መግለጻቸውን ሲፒጄ በመግለጫው አካቷል።
