12ኛው የአፍሪካ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጉባኤ በዛሬው ዕለት በጋና አክራ ዓለማቀፍ የስብሰባ ማዕከል የተከፈተ ሲሆን፤ ከመላው አፍሪካና ካሪቢያን አገራት የተውጣጡ የፖለቲካ መሪዎች፣ ፖሊሲ አውጪዎችና ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉበት ነው፡፡
በጉባኤው ላይ የብልፅግና ፓርቲ ም/ፕሬዚዳንት እና የዋና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አደም ፋራህና የብልፅግና ፓርቲ የዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ ሚኒስትር ዶ/ር ቢቂላ ሁሪሳ እየተሳተፉ እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ከዛሬ ጀምሮ ለተከታታይ ሦስት ቀናት የሚካሄደው የአፍሪካ ፖለቲካ ፓርቲዎች ጉባኤ፤ በቀጠናዊ ትስስር፣ በሰላምና ፀጥታ፣ በሁሉን አቀፍ አስተዳደር፣ በዘላቂ የኢኮኖሚ እድገትና የፖለቲካ ፓርቲዎች ሚና በአህጉራዊ ልማት አጀንዳዎች ላይ በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ይመክራል ተብሏል።
ጉባኤው በአህጉሪቱ ዲሞክራሲያዊ አስተዳደርና የፖለቲካ ትብብርን ለማጠናከር ያለመ የውይይት፣ የትብብር እና የሃሳብ ልውውጥ መድረክን የሚፈጥር እንደሚሆንም ተጠቁሟል፡፡
የመድረኩ አዘጋጆች እንደገለጹት፤ ጉባኤው በፓርቲዎች መካከል ውይይትን ለማጎልበት፣ አህጉራዊ አንድነትን ለማጠናከርና በጋራ ቅድሚያ በሚሰጣቸው ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባት ለመፍጠር፣ እንደ የአየር ንብረት ለውጥ፣ ስደትና የህዝብ ጤና ያሉ ድንበር ዘለል ተግዳሮቶችን ለመፍታት ያለመ ነው፡፡
