የጀርመን ዐቃቤ ሕግ ቢሮ “ብርጌድ ንሓመዱ” የተባለ “ሽብርተኛ ቡድን” በመመሥረት እና አባል በመሆን በተጠረጠሩ ሰዎች ላይ ከፍተኛ አሰሳ መካሔዱን አስታወቀ። ብርጌድ ንሓመዱ
“የኤርትራ መንግሥትን ለመጣል ያለመ ዓለም አቀፍ ትሥሥር ያለው ኔትወርክ” እንደሆነ መቀመጫውን በካርልስሩኸ ያደረገው የጀርመን ዐቃቤ ሕግ ቢሮ አስታውቋል።
በ17 ተጠርጣሪዎች ላይ በስድስት የጀርመን ፌድራል ግዛቶች በሚገኙ 19 ቦታዎች አሰሳ የተካሔደው ትላንት ረቡዕ ነው። ተመሳሳይ አሰሳ በዴንማርክ ጭምር መካሔዱን የጀርመን ዐቃቤ ሕግ ቢሮ አስታውቋል።
በጀርመን በተካሔደው አሰሳ ከ200 በላይ የፖሊስ መኮንኖች ተሳትፈዋል። በመግለጫው መሠረት በቁጥጥር ሥር የዋለ ተጠርጣሪ የለም። አሰሳው ያነጣጠረባቸው ተጠርጣሪዎች “ብርጌድ ንሓመዱ” ውስጥ ከፍተኛ የአመራርነት ቦታ ያላቸው መሆናቸውን የምርመራ ውጤቶች እንደሚያሳዩ መሥሪያ ቤቱ አስታውቋል።
“ብርጌድ ንሓመዱ” በሔሰን ግዛት በምትገኘው ጊሰን ከተማ ዉስጥ በጎርጎሮሳዊው ነሐሴ 2022 እና መስከረም 2023 የኤርትራ የባሕል ፌስቲቫል ላይ የተቀሰቀሱ ኃይለኛ ኹከቶችን በማደራጀት ይወነጀላል። በመስከረም 2023 በሽቱትጋርት ከተማ በኤርትራውያን ማኅበር ስብሰባ ላይ ለተፈጠረ ኹከትም “ብርጌድ ንሓመዱ” ተጠያቂ ይደረጋል። በኹከቶቹ በርካታ የፖሊስ መኮንኖች መጎዳታቸውን የጀርመን ዐቃቤ ሕግ ቢሮ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።
Dw
