የሶፍ ዑመር የባቡር መንገድ ግንባታ በተያዘው ዓመት ይጠናቀቃል
በሶፍ ዑመር ዋሻና ሎጅ ፕሮጀክቶች ውስጥ ለቱሪስት አገልግሎት መስጫ እየተገነባ የሚገኘው የባቡር መስመር በተያዘው ዓመት እንደሚጠናቀቅ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን አስታወቀ።
የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የባቡር ዘርፍ ምክትል ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ስለሺ ካሳ እንደገለጹት፤ የባሌ አካባቢን ቱሪዝም ለማሳደግ ሶፍ ዑመር ላይ እየተገነባ ያለው የባቡር መንገድ ግንባታ በዚህ ዓመት ይጠናቀቃል።
ኢትዮጵያ ከአሏት ዕምቅ ሀብቶች መካከል አንዱ ቱሪዝም ነው ያሉት ኢንጂነር ስለሺ፤ ሀገሪቱን ባላት የቱሪዝም ሀብት ልክ ተጠቃሚ ለማድረግ በትራንስፖርት ማስተሳሰር ቀዳሚ አጀንዳ መሆኑን ጠቁመዋል።
በውስጥ አቅም በመገንባት የመጀመሪያ የሆነው ይህ ፕሮጀክት እስካሁን ከ50 በመቶ በላይ መጠናቀቁን ገልጸው፣ አጠቃላይ ርዝመቱ አምስት ኪሎ ሜትር መሆኑን አስረድተዋል።
የባቡር መንገዱ በቀጣይም እንደ ሁኔታው ሊሰፋ የሚችልበት ዕድል መኖሩን ጠቅሰው፤ ለጎብኝዎች ያለ ስጋት መንቀሳቀስ የሚያስችል መሆኑን አብራርተዋል።
በሀገሪቱ በአጠቃላይ የባቡር መስመሮች ላይ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን የጠቀሱት ኢንጂነር ስለሺ፤ አዋሽ – ኮምቦልቻ – ሀራ ገበያ የባቡር መንገድ ከዚህ በፊት የነበረውን የመሠረተ ልማት ስርቆት ችግር በመቅረፍ ከአማራና ከአፋር ክልሎች ጋር በተሰራ ስራ መቀነስ መቻሉን አያይዘው አመልክተዋል።
የባቡር መስመሩ አገልግሎቱን ለማስጀመር በውስጥ አቅም የመጠገን ተግባራት እየተከናወኑ ሲሆን፤ በቅርቡም ወደ ስራ ለማስገባት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
ጋዜጣ ፕላስ
