– ፀረ-አበረታች ቅመሞች ባለስልጣን
በ2017 ዓ.ም የፀረ-አበረታች ቅመሞች የሕግ ጥሰት የፈጸሙ አምስት አትሌቶች ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ መውሰዱን የኢትዮጵያ ፀረ-አበረታች ቅመሞች ባለ ስልጣን ይፋ አድርጓል፡፡
የባለ ስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር መኮንን ይደርሳል፣ ምርመራ ከተደረገለቻው 1196 አትሌቶች ሶስቱ አበረታች መድሀኒት ተጠቅመው በመገኘታቸው፣ ከሁለት እስከ ሶስት ዓመት ድረስ በማንኛውም ስፖርታዊ እንቅስቃሴ እንዳይካፈሉ መታገዳቸውን አሳውቀዋል፡፡
ሌሎች ሁለት አትሌቶችም ናሙና ለመስጠትና የአድራሻ ምዝገባ ለማድረግ ተባባሪ ባለመሆናቸው አስተዳደራዊ እርምጃ እንደተወሰደባቸውም ተናግረዋል፡፡
በተጨማሪም በቅርቡ በሚጀመረው 20ኛው የቶኪዮ ዓለም አትሌቲከስ ሻምፒዮና የተቀመጡ መስፈርቶችን ለማሟላት፣ ለ143 አትሌቶች ምርመራ ተደርጎ ሁሉም ማለፋቸውን ዋና ዳይሬክተሩ ይፋ አድርገዋል፡፡
በሌላ በኩል የአትሌት ባዮሎጂካል ፓስፖርት ላብራቶሪ ለማቋቋም የተደረገው ጥረት የተሳካ እንደነበር የገለጹት አቶ መኮንን ይደርሳል ላብራቶሪውን ወደ ስራ ለማስገባት፣ የዓለም አቀፉን የጸረ አበረታች ቅመሞች ኤጄንሲ ይሁንታ እየተጠባበቁ እንደሚገኙም ተናግረዋል፡፡
በ2018 በጀት ዓመት ከ750 ሚሊዮን ብር በላይ በመመደብ አዲስ የተሟላ የመመርመሪያ ላብራቶሪ ለመገንባት ስራዎች መጀመራቸውንም አሳውቀዋል፡፡#EBC
