የዛሬ ስኬታችሁ የሚለካው በራሳችሁ የእውቀት ማማ ሳይሆን ለኢትዮጵያና ለህዝቧ በምታደርጉት አስተዋጽኦ ነው ሲሉ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት አምባሳደር ታዬ አፅቀስላሴ ገለፁ።
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለ75ኛ ዙር በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች የምርቃት ስነስርዓት እና የተቋቋመበትን የአልማዝ ኢዮቤልዩ በዓል በዛሬው ዕለት በማክበር ላይ ይገኛል።
በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት አምባሳደር ታዬ አፅቀስላሴ፤ ተመራቂ ተማሪዎች በርካታ እንቅልፍ አልባ ሌልቶችን አሳልፋችሁ ለዚህ ቀን በመብቃታችሁ የእንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።
የዛሬ ስኬታችሁ የሚለካው በራሳችሁ የእውቀት ማማ ሳይሆን ለኢትዮጵያና ለህዝቧ በምታደርጉት አስተዋጽኦ ነው ሲሉም ገልጸዋል።
ዩኒቨርሲቲው በሀገሪቱ የህይወት ኡደት ላይ ሲሰራና ሲመራመር መቆየቱን አስታውሰው፤ የኢትዮጵያ የእውቀትና የስነጥበብ ማህደር መሆኑን ተናግረዋል።
እንዲሁም ዩኒቨርሲቲው ከኢትዮጵያ አልፎ ሌሎችም ሀገራትም ጭምር የእውቀት ምንጭ በመሆን እያገለገለ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።
የችግሮቻችን መፍትሔ ሁሉ በሩቅ ጠበብቶች እጅ እንዳለ በሚወሳበት ወቅት የመፍትሔ ሀሳቦችን በማፍለቅ ለሀገር እድገት አስተዋጽኦ ሲያደርግ መቆየቱን ፕሬዚዳንቱ ገልጸዋል።
የዛሬ ተመራቂዎች ስለዓለም ኢኮኖሚ እድገት፣ ጂኦፖለቲካና ስለተዋዋጭ ዓለም አሁናዊ ሁኔታ በማንበብ በኢትዮጵያ ዓይን በመተርጎም ለሀገር እድገት መትጋት እንደሚገባ ተናግረዋል።
“ይህ ቀን እውን እንዲሆን እንቅልፍ ያጣችሁና ከጉርሻችሁ ያካፈላችሁ ወላጆች እንኳን ደስ ያላችሁ” ብለዋል።
በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሀኑ ነጋን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ የተመራቂ ወላጆች፣ የዩኒቨርሲቲው የቦርድ አመራሮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
