የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አባስ አራግቺ ኑክሌር ማበልጸጉን መቀጠል ‹‹የሀገር ኩራት›› ጉዳይ ነው ብለዋል፡፡
የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ፤ቴህራን ባለፈው ወር በአሜሪካ እና በእስራኤል የአየር ጥቃቶች ከፍተኛ ጉዳት የደረሰበትን የዩራኒየም ማበልጸግ ፕሮግራሟን ማቆም እንደማትችል ተናግረዋል።
አራግቺ ከአሜሪካው ፎክስ ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ፤‹‹በእርግጥም የደረሰው ጉዳት ከባድ በመሆኑ አሁን ቆሟል፤ ነገር ግን ማበልጸጋችንን ማቆም አንችልም ምክንያቱም ይህ የራሳችን ሳይንቲስቶች ውጤት ነው፤ከዚህም በላይ የሀገር ኩራት ጉዳይ ነው››ብለዋል።
አራግቺ በቃለ ምልልሱ መጀመሪያ ላይ ኢራን ከአሜሪካ ጋር ለውይይት ክፍት መሆኗን ገልጸው፤ነገር ግን ለጊዜው ቀጥተኛ ንግግሮች እንደማይኖሩ ተናግረዋል፡፡
ለጋራ ተጠቃሚነት መፍትሄ የሚመጡ ከሆነ ከእነሱ ጋር ለመነጋገር ዝግጁ ነኝ ብለዋል።
የኢራን የኑክሌር ፕሮግራም ሰላማዊ መሆኑን እና ለዘላለምም ሰላማዊ ሆኖ እንደሚቀጥል፤ኢራን በጭራሽ የኑክሌር ጦር መሳሪያ እንደማትፈልግ ለማረጋገጥ የሚያስፈልገውን ማንኛውንም የመተማመኛ እርምጃ ለመውሰድ ዝግጁ ነን ሲሉ ገልጸዋል፡፡
በምላሹም ማዕቀባቸውን እንዲያነሱ እንጠብቃለን ፤ስለዚህ ለአሜሪካ የማስተላልፈው መልዕክት የኢራንን የኑክሌር ፕሮግራም በተመለከተ በድርድር መፍትሄ እንፈልግ የሚል ነው ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አክለዋል።
የአራግቺ አስተያየት የአሜሪካዉ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቅርብ እንደሚከታተሉት በሚታወቀው ፎክስ ኒውስ ላይ የተላለፈዉ የ16 ደቂቃ ቃለ ምልልስ አካል ነበር ሲል አልጀዚራ ዘግቧል።
