አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በደቡብ ኮርዶፋን ግዛት በደርዘን የሚቆጠሩ ህጻናትን እና ንጹሃን ዜጎችን ለህልፈት የዳረጉ ጥቃቶችን የሚጠቁሙ ሪፖርቶች “እጅግ እንዳሳሰቧቸው” የተባበሩት መንግሥታት ቃል አቀባይ በመግለጫቸው አስታውቀዋል።
መግለጫው ህዳር 25 ቀን በካሎጊ ከተማ ውስጥ አማጺው ፈጥኖ ደራሽ ኃይል በሁለት የድሮን ጥቃቶች መዋለ ሕጻናት መምታቱን እና ሦስተኛው ደግሞ ሆስፒታል ላይ ማረፉን ተከትሎ የመጣ ነው። የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንደገለጸው፤ ይህ ጥቃት 79 ንጹሃን ዜጎችን የገደለ ሲሆን ከነዚህም መካከል 43 ህጻናት ይገኙበታል።
በሌላ በኩል በተመሳሳይ ቀን በሰሜን ኮርዶፋን በዓለም ምግብ ፕሮግራም የሰብዓዊ እርዳታ ጭነት ላይ የአየር ጥቃት ተፈጽሞ አሽከርካሪው ላይ ከባድ የመቁሰል አደጋ ደርሶበታል ተብሏል።
“ዋና ፀኃፊው ከፍተኛ የእርዳታ ፍላጎት ባለበት በዚህ ወቅት በሰብዓዊ እርዳታ ተግባራት ላይ በተፈጸመው ተጨማሪ ጥቃት አዝነዋል” ሲሉ ቃል አቀባዩ ገልፀዋል
ጉቴሬዝ ትምህርት ቤቶችን እና ሆስፒታሎችን ኢላማ ማድረግ ዓለም አቀፍ ሕግን በእጅጉ የሚጥስ ሊሆን እንደሚችል አጽንኦት በመስጠት፤ ውጊያው ወዲያውኑ እንዲገታ፣ የጦር መሳሪያ ዝውውር እንዲቆም እና ያልተገደበ የሰብዓዊ እርዳታ እንዲፈቀድ ጥሪ አቅርበዋል።
