ኬንያ በዓመት ሁለት ጊዜ ብቻ በመወሰድ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ /ከ99 በመቶ በላይ/ መከላከያ የሚሰጠውን አዲስ የኤችአይቪ መከላከያ መድኃኒት በመጋቢት ወር ላይ ማሰራጨት ትጀምራለች።
በጊሊያድ ሳይንሰስ ኩባንያ የሚመረተው ሌናካፓቪር የተሰኘው መድኃኒት፣ የኤችአይቪ ቫይረስ የመተላለፍ እድልን ከ99.9 በመቶ በላይ ይቀንሳል።
ኬንያ ከግሎባል ፈንድ ጋር ባደረገችው ስምምነት መሰረት የመጀመሪያውን ዙር 21 ሺህ የመድኃኒት መጠን ተረክባለች።
የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ አደን ዱዋሌ፤ የመጀመሪያው ምዕራፍ 15 ግዛቶችን በማካተት በመጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ ይጀምራል ሲሉ ያስታወቁ ሲሆን፤ ተጨማሪ 12 ሺህ የመድኃኒት መጠኖች እስከ ሚያዝያ ወር ድረስ ይጠበቃሉ ብለዋል።
መድኃኒቱን የማዳረስ ስራው የተጀመረው የአፍሪካ ሀገራት በፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ስር ከሚደረገው የእርዳታ ቅነሳ ጋር እየታገሉ ባሉበት ወቅት ነው።
በዓለም ዙሪያ ከሚኖሩ 40.8 ሚሊየን ኤችአይቪ በደማቸው ውስጥ ካለባቸው ሰዎች መካከል 52 በመቶ የሚሆኑት በምስራቅ እና በደቡብ አፍሪካ የሚገኙ ናቸው።
አሜሪካ 3.7 በመቶ የኤችአይቪ ስርጭት መጠን ላላት ኬንያ ተጨማሪ 25 ሺህ የመድኃኒት መጠኖችን ለመስጠት ቃል ገብታለች።
በታህሳስ ወር ኬንያ ከአሜሪካ ጋር የ2.5 ቢሊየን ዶላር የሁለትዮሽ የጤና ስምምነት ተፈራርማለች፤ ይህም ትራምፕ USAIDን ካፈረሱ በኋላ የተደረገ የመጀመሪያው ስምምነት ነው።
በስምምነቱ መሰረት ዋሽንግተን በአምስት ዓመታት ውስጥ 1.6 ቢሊየን ዶላር የምታቀርብ ሲሆን፤ ኬንያ በበኩሏ 8መቶ50 ሚሊየን ዶላር በማዋጣት ቀስ በቀስ ኃላፊነት ትረከባለች ያለዉ አፍሪካ ኒዉስ ኢንግሊሽ ነዉ።
