የኤርትራ መንግሥት በእምነታቸው ምክንያት ለእስር ተዳርገው የቆዩ በርካታ የወንጌላውያን እምነት ተከታዮችን ከእስር መልቀቁ ተሰምቷል ።
ባለሥልጣናት እንደገለጹት፤ ቁጥራቸው ከ40 የሚበልጡ ሰዎች ከአሥመራ አቅራቢያ ከሚገኘው ማይ-ሰርዋ ወታደራዊ እስር ቤት ባለፉት ቀናት ውስጥ ተለቅቀዋል።
መንግሥት ክልከላ ጥሎባቸው ከነበሩ የክርስትና ቤተ እምነቶች የተውጣጡ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከእስር እየተለቀቁ ሲሆን፤ ባለፈው ጥር ወር 13 እንዲሁም በኅዳር ወር 100 የሚጠጉ አማኞች መፈታታቸው ይታወሳል።
ባለፉት ወራት ከሃይማኖት ተከታዮች በተጨማሪ ለ18 ዓመታት የታሰሩ ነጋዴዎችና የፀጥታ ኃይል አባላትም ከማይ-ሰርዋ እስር ቤት መለቀቃቸው ተመልክቷል።
የኤርትራ መንግሥት ከ20 ዓመታት በፊት በርካታ የእምነት ተቋማትን በይፋ በማገድ መሪዎቻቸውንና ተከታዮቻቸውን ማሰሩ አይዘነጋም።
