የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር ኢዝራኤል ካትዝ በሰጡት መግለጫ የአገሪቱ ጦር ኢራን መሪዎችን ማደኑን እንዲቀጥል ከጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔትያናሁ ትዕዛዝ መሰጠቱን ተናገሩ።
እስራኤል ሰኞ ሌሊት በፈጸመቻቸው ጥቃቶች ከፍተኛ የኢራን የደኅንነት ኃላፊ የሆኑትን አሊ ላሪጃኒን መግደሏን ገልጻለች። ባለሥልጣኑ የተገደሉት ከልጃቸው ጋር በተደበቁበት አፓርትመንት ውስጥ እንደሆነ የእስራኤል መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።
በተጨማሪም የእስራኤል ጦር ‘ባሲጅ’ የተባለው የኢራን ታጣቂ ኃይል አዛዥ የሆኑትን ጎላምሬዛ ሶሊማኑን መግደሏን አስታውቃለች። የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ፤ ከኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጋር ግንኙነት ያለውን ታጣቂ ቡድን ላለፉት ስድስት ዓመታት ሲመሩ ቆዩትን ወታደራዊ አዛዥ ተገድለዋል ብሏል።
አዛዡ የሚመሩት ታጣቂ ቡድን ታኅሣሥ ላይ የነበረውን ፀረ መንግሥት ተቃውሞ ለማፈን በተወሰደው በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የተገደሉበት ዘመቻ ውስጥ ተሳትፎ ነበረው።
የመከላከያ ሚኒስትሩ ካትዝ፤ የኢራኑ ከፍተኛ የደኅንነት ባለሥልጣን መገደላቸውን ባስታወቁበት መግለጫ “ጠቅላይ ሚኒስትሩ እና እኔ የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት የኢራንን የሽብር እና የጭቆና አገዛዝ አመራሮች ማደኑን እንዲቀጥል ትዕዛዝ ሰጥተናል” ብለዋል።
“የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ትራምፕ የኢራን አመራሮች በከፍተኛ መጠን ስለ መለዋወጣቸውን ሲናገሩ ነበር … ከቀሩት ከፍተኛ አመራሮች መካከል ሁለቱ ስለተገደሉ የአመራሮች መለዋወጡ እንደቀጠለ መረጃ እናደርሳቸዋለን” ሲሉ ተናግረዋል።
እስራኤል ይሄንን ብትልም እስካሁን ድረስ ላሪጃኒ እና ሶሎማኒ ስለመገደላቸው ከኢራን በኩል ማረጋገጫ አልተሰጠም።
BBC
